የሲዳማ ቡና እና መቐለ 70 እንደርታ ጨዋታ ያለ ጎል ሲጠናቀቅ የመጨረሻ ደቂቃ ድራማን የነበረው የነገሌ እና አዳማ ጨዋታ በነገሌ አርሲ አሸናፊነት ተጠናቋል።
ሲዳማ ቡና 0-0 መቐለ 70 እንደርታ
የሊጉን መሪ ሲዳማ ቡና እና መቐለ 70 እንደርታን ባገናኘው ጨዋታ ጎል ሳይቆጠር ተጠናቋል። በርካታ ጥፋቶችን ከማስተናገድ ውጪ በይበልጥ ፉክክሮችን ያላስመለከተን የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በንፅፅር በመጀመሪያው አጋማሽ ሲዳማ ቡናዎች የተሻለውን እንቅስቃሴ ማድረግ ቢችሉም ጎል ማስቆጠር ግን ያልቻሉበት ነበር።
ከመጀመሪያው አጋማሽ አኳያ ጥሩ መልክን የተላበሰው ሁለተኛው አጋማሽ ሲዳማ ቡናዎች በይበልጥ ከፍ ባለ መነቃቃት እና የግብ መንገዶችን ለመፍጠር ጥረት ያደረጉበት ቢሆንም 74ኛው ደቂቃ ላይ ዘረሰናይ ብርሀነ በመቐለ በኩል በሁለት ቢጫ ካርድ በቀይ ከመውጣቱ ውጪ ጨዋታው በጎሎች መታጀብ ሳይችል 0ለ0 ተቋጭቷል።
- ማሰታውቂያ -

ነገሌ አርሲ 2-1 አዳማ ከተማ
የመጨረሻ ደቂቃ ድራማዎችን ያስመለከተን የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ጨዋታ በቀዳሚው አጋማሽ አዳማዎች በኳስ እንቅስቃሴ ብልጫውን መያዝ ቢችሉም በሙከራ ረገድ ሻል ያለሉት ነገሌ አርሲዎች በከቤ ብዙነህ እና አለኝታ ማርቆስ አማካኝነት ሙከራን ቢያደርጉም ያለ ጎል አጋማሹ መገባደድ ችሏል።
እጅግ በድራማዊ ሁነቶች የደመቀው ሁለተኛው አጋማሽ እንደተለመደው ነገሌ አርሲዎች በብዙ ረገድ ብልጫውን ለመውሰድ ጥረት ያደረጉበት መሆን ቢችልም 83ኛው ደቂቃ ላይ አዳማ ከተማዎች መሪ መሆን ችለዋል። ከሀይደር ሸረፋ ያገኘውን ኳስ አህመድ ሁሴን ወደ ጎልነት ቀይሮ ቡድኑ ቀዳሚ ያደረገ ቢሆንም ጨዋታው ተጠናቆ በተሰጠው አምስት ጭማሪ ደቂቃዎች ውስጥ ግን ነገሌ አርሲ በቅያሪ ተጫዋቾች ዕገዛ ጎሎች ያስቆጠሩበት ነበር።
90+2 ተቀይሮ የገባው ገብረመስቀል ዱባለ ያቀበለውን ኳስ ሮህበት ሰለሎ ወደ ጎልነት ቀይሮ ጨዋታውን ወደ 1ለ1 ሲቀይር የዳኛው ፊሽካ በሚጠበቅበት ወቅት በጨዋታው ድንቅ የነበረው ከቤ ብዙነህ በአግባቡ ከግራ መስመር ያቀበለውን ኳስ ገብረመስቀል ዱባለ ጎል አድርጎት በመጨረሻም ነገሌ አርሲዎች ጨዋታውን 2ለ1 አሸንፈው ወጥተዋል።


