በትልቁ ትግራይ ስታድየም በተካሄደው 27ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ መቐለ ከተማ በኣማኑኤል ገብረሚካኤል ብቸኛ ግብ ታግዞ ወሳኝ ሥስት ነጥብ ኣሳክቷል። መቐለዎች ፋሲልን ከገጠመው ቡድን ያሬድ ብርሃነን በያሬድ ከበደ ቀይረው ሲገቡ መከላከያዎች በጅማ ከተሸነፈው ቡድን 4 ቅያሪዎችን አድርገዋል። እነዚህም በረኛው ይድነቃቸው ኪዳኔን በኣቤል ማሞ፣ ማራኪ ወርቁን በሳሙኤል ሳሊሶ፣ ምንይሉ ወንድሙን በኣቤል ከበደ እንዲሁም በሃይሉ ግርማን በኣማኑኤል ተሾመ ቀይረው ገብተዋል።

የመጀመርያው ኣጋማሽ መከላከያዎች ወደ ኋላ በማፈግፈግ መቐለዎች ኳስ እንዲይዙ በመፍቀድ ኣማካዩ ኣማኑኤል ተሾመ በሚጥላቸው ረጃጅም ኳሶች መልሶ ማጥቃትን ለማስጀመር ሲሞክሩ ታይቷል። ሆኖም በረጅሙ የሚጣሉ ኳሶች ብቻውን ተነጥሎ ሲጫወት የነበረውን ፍፁም ገ\ማርያም ኢላማ ቢያደርጉም በመቐለ ተከላካዮች በቀላሉ ሲቆጣጠሩት ነበር። ሆኖም ፍፁም በግሉ በሚያደርገው ጥረት የመቐለን ግብ ክልል ሲፈትን ነበር። የዚህም ውጤት በ10ኛው ደቂቃ ከግራ መስመር ወደ ውስጥ ሰብሮ በመግባት የሞከረው ኳስ የቋሚ ብረቱ ታች መልሶበታል። መቐለዎች የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስዱም ወደ ኋላ ኣፈግፍጎ ሁለት መስመር በመስራት ሲከላከል የነበረውን የመከላከያ ኣማካይ እና ተከላካይ ክፍልን ሰብረው መግባት ኣልቻሉም። በተለይም በቀጥታ ከመሀል ሜዳ የሚላኩ ኳሶች ምንም ሊፈይዱ ኣልቻሉም። ከመሀል ሜዳ ከተላኩት ኳሶች የተሻለ የነበረው 23ኛው ደቂቃ ላይ ኣመለ በረጅሙ የላካትን ኳስ ኣማኑኤል ፍጥነቱን ተጠቅሞ ለማለፍ ቢሞክርም ንቁ ሆኖ ሲከላከል የነበረው ሙሉቀን ደሳለኝ ኣጨናግፎበታል። መቐለዎች የመከላከያን ጥብቅ መከላከል በመመልከት የማጥቃት ኣቅጣጫቸውን በግራ መስመር ሲጫወት በነበረው ፋሲይኑ ኑሁ በማድረግ የጎል ዕድሎችን መፍጠር ችለዋል። ለዚህ ማሳያ በ25ኛው ደቂቃ ፋሲይኒ ከግራ መስመር ያሻማው ኳስ ያሬድ ከበደ በጭንቅላቱ ቢገጨውም በጎሉ ኣናት ወጥቷል። በተመሳሳይ በ29ኛው ደቂቃ ፋሱይኒ ከማዕዘን ምት ተሻግራ በተከላካዮች ተግጭታ የመጣችውን ኳስ በግራ እግሩ ኣክርሮ ቢመታውም ኢላማውን የጠበቀ መሆን ኣልቻለም። ተደጋጋሚ የግብ ሙከራ ያደረጉት መቐለዎች ቢሆኑም ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ ሳያደርጉ የመጀመርያው 45 ሊጠናቀቅ ተገዷል።

ሁለተኛው ኣጋማሽ እንደ መጀመርያው ኣጋማሽ በተመሳሳይ መቐለዎች በማጥቃት መከላከያዎች በመከላከል ቀጥለዋል። በመጀመርያው ኣጋማሽ መጨረሻ የተጎዳውን ጋቶች ፓኖምን ቀይሮ የገባው ሃብታሙ ተከስተ ከኣጥቂው ጀርባ በመሆን እንዲሁም ወደ ግራ መስመር በመውጣት እድሎችን ሊፈጥር ቢሞክርም መጨረሻቸው ሊሳካ ኣልቻለም።
መቐለዎች በሁለተኛው አጋማሽ የመጀመርያ ኢላማውን የጠበቀ ሙከራቸውን ለማድረግ የፈጀባቸው 2ደቂቃዎች ብቻ ነበሩ። በ47ኛው ደቂቃ ላይ ኣመለ ከ ሚኪኤለ የተቀበለውን ኳስ በቀጥታ ወደግብ ቢመታውም የመከላከያው ግብ ጠባቂ ኣቤል በቀላሉ ተቆጣጥሮታል። ከሚያገኙት የቆሙ ኳሶች የጎል ሙከራ ለማድረግ ሲሞክሩ የነበሩት መከላከያዎች በ51ኛው ደቂቃ በግምት ከ40 ሜትር ያገኙትን ቅጣት ኣማኑኤል ተሾመ ኣክርሮ ቢመታውም ኦቮኖ እንደምንም ኣድኖበታል። መቐለዎች በተደጋጋሚ የሜዳው ሶስተኛ ክፍል ቢደርሱም የመከላከያ ተከላካይ ክፍልን ሊሰብሩት ኣልቻሉም። ከተደጋጋሚ ሙከራ በኋላ በ72ኛው ደቂቃ ከ ያሬድ ከበደ መሬት ለመሬት የተላከውን ሰንጣቂ ኳስ ኣማኑኤል ከተከላካዮቹ መሃል ሾልኮ በማምለጥ የመጀመርያውን ጎል ኣስቆጥሯል። ከጎሉ መቆጠር በኃላ መከላከያዎች ኣማኑኤል ኳሱን በሚይዝበት ግዜ ጥፋት ሰርቷል በሚል ከዳኛው ጋር በፈጠሩት ሰጣ ገባ ጨዋታው ለ 6 ደቂቃዎች ተቋርጦ ነበር።

ከጎሉ መቆጠር በኃላ መከላከያዎች ኣማካዩን ኣማኑኤል ተሾመን በኣጥቂው የተሻ ግዛው ቢቀይሩም ውጤቱን መቀየር ኣልቻሉም። በዚህም በውጥረት ታጅቦ ይተካሄደው ጨዋታ በመቐለ ከተማ 1-0 አሸናፊነት ተጠናቋል። ውጤቱንም ተከትሎ መቐለ ከተማ ነጥቡን 46 በማድረግ ከመሪዎቹ ጅማ አባጅፋር እና ቅ/ጊዮርጊስ በ2ነጥቦች ብቻ በማነስ 3ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ መከላከያ በአንፃሩ በ32 ነጥቦች 10ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።


