የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ክለብ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ካደረጉት ጨዋታ አስቀድሞ ለሊግ ካምፓኒው በጻፈው ደብዳቤ ዙሪያ የፕሪሚየር ሊጉ አክሲዮን ማህበር ሲዳማ ቡናን አስጠነቀቀ።
አክሲዮን ማህበሩ ሲዳማ ቡና የዳኛ ዕጥረት ያለ ይመስል ኢንተርናሽናል አርቢትር በአምላክ ተሰማ ሌላ ጨዋታ ካጫወተ 48 ሰአት ሳይሞላው መመደቡ ቅሬታ እንደፈጠረበት በተጨማሪም አርቢትሩ በግሉ የቅዱስ ጊዮርጊስ ደጋፊ በመሆኑ ከጨዋታው ምደባ እንዲቀየር ያቀረበውን ጥያቄ ተቀባይነት የሌለው ሲል ሊግ ካምፓኒው አጣጥሎታል።
ሊግ ካምፓኒው ለክለቡ ጥያቄ በሰጠው ምላሽ
“የዳኛ ይቀየርልን ጥያቄ በማንኛውም መስፈርት ህጋዊ አለመሆኑን ዳኛው ይቀየርልን የተባለው መረጃና ማስረጃ ሳይኖረው መሆኑ የዳኛውን ስነልቦና የሚጎዳና በህግ የሚያስጠይቅ ክለቡን ለከባድ ቅጣት የሚዳርግ ነው” ሲል አስረድቷል። በተጨማሪም “ከጨዋታው በኋላ አድልዎ አድርጎብናል የሚለው አቤቱታ የተጣሰውን የህግ አንቀጽ በመጥቀስ መክሰስ ሲገባው ባለመፈጸሙ የቀረበውን አቤቱታ አወዳዳሪው አካል አልተቀበለውም” በማለት ጥያቄያቸው ውድቅ መደረጉን ገልጿል።
ሊግ ካምፓኒው አጽንኦት ሰጥቶ በሰጠው ምላሽ ከደንብና ከመመርያ ውጪ የሚመጡ አቤቱታዎችን እንደማይቀበል ክለቡ ተመሳሳይ ድርጊት ፈጽሞ ከተገኘ አስፈላጊ የተባለውን የዲሲፕሊን ርምጃ እንደሚወስድ በመግለጽ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።
አስተያየት ይስጡ