የፕሪምየር ሊጉን በቅርቡ የተቀላቀለው አዲስ አበባ ከተማ ሲሳይ ደምሴ እና ሮቤል ግርማን አስፈረመ
-የሶስት ተጨዋቾቹን ውል አራዝሟል
የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግን በቅርቡ የተቀላቀለው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እግር ኳስ ቡድን በመጪው ዓመት በተጠናከረ መልኩ ለመቅረብ ሰባት ተጨዋቾችን ሊያስፈርም ችሏል፤ የኢትዮጵያ ከፍተኛው ሊግ ላይ በተመሰረተ እና ውድድሩም ውስጥ በገባ የአምስት ዓመታት የምስረታው ጊዜ የከፍተኛ ሊጉን በሶስተኛነት በማጠናቀቅ ለመጀመሪያ ጊዜ ፕሪምየር ሊጉን ለመቀላቀል የቻለው አዲስ አበባ ከተማ ይህንን ስኬት ለማግኘት የቻለው ቡድኑን ለመጀመሪያ ጊዜ በተረከበው አሰልጣኝ ስዩም ከበደ አማካይነት ሲሆን ክለቡ በመጪው ዓመት ተጠናክሮ ለመቅረብ ባለው ፍላጎት ከአፍሪካ አህጉር የውጪ ተጨዋቾችን ለማምጣት ሀሳብ እንዳለውም ታውቋል፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እግር ኳስ ቡድን በእዚሁም መሰረት ካስፈረማቸው ሰባት ተጨዋቾች ውስጥ ከኢትዮጵያ ቡና ጋር በ2003 የፕሪምየር ሊጉን ዋንጫ ያነሳውን የቀድሞ የቅዱስ ጊዮርጊስ፣ የኒያላ፣ የመከላከያ፣ የድሬዳዋ ከተማ እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጨዋች ሲሳይ ደምሴ እና እንደዚሁም ደግሞ የኤሌክትሪክ፣ የሲዳማ ቡና፣ የኢትዮጵያ ቡና፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን፣ ደደቢት እና በእዚህ ዓመት ደግሞ ፋሲል ከተማን ወደ ፕሪምየር ሊግ እንዲገባ ትልቁን አስተዋፅኦ ካደረጉት ተጨዋቾች መካከል አንዱ የሆነውን ሮቤል ግርማን ሊያስፈርም ችሏል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ እግር ኳስ ቡድን በእዚህ የዝውውር መስኮት ሲሳይ ደምሴን ለሁለት ዓመት ሲያስፈርም 1.5 ሚሊየን ብር ክፍያ የፈፀመለት ሲሆን ይህም ወደ ደመወዝ ሲመነዘር 68ሺ 181 ብር ይሆናል፤
- ማሰታውቂያ -
ለሮቤል ግርማ ደግሞ 1.4 ሚሊየን ብር ክፍያ ለሁለት ዓመት የተፈፀመለት ሲሆን ወደ ደመወዝ ሲመነዘር 63ሺ 636 ብር ይሆናል፤ ክለቡ ከእነዚህ ተጨዋቾች ውጪ ያስመጣቸው ተጨዋቾችም ዴሜጥሮስን ከአዳማ ከተማ ለሁለት ዓመት በ1.3 ሚሊየን ብር ወደ ደመወዝ ሲቀየር 59 ሺ 90 ብር፣ ግብ ጠባቂው ደረጄ ዓለሙን ከዳሽን ቢራ ለሁለት ዓመት በ1.3 ሚሊየን ብር 380 ሺ ወደ ደመወዝ ሲቀየር 62ሺ 727 ብር፣ ፀጋን ከወላይታ ዲቻ በ1.3 ሚሊየን ብር ለሁለት ዓመት ወደ ደመወዝ ሲቀየር 59ሺ 90 ብር፣ ኤርሚያስን ከሱሉልታ ከተማ ለሁለት ዓመት በደመወዝ 45ሺ 454 ብር፣1 ከነዓንን ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ በ800 ሺ ብር ለሁለት ዓመት ወደ ደመወዝ ሲቀየር በ36 ሺ 363 ብር ሲያስፈርም የሶስት ተጨዋቾችን ውል ደግሞ አራዝሟል፡፡ በእዚሁም መሰረት ከነባር ተጨዋቾች ውስጥ በጥሩ ብቃታቸው ክለቡ ዮናታን ብርሃነን ለአንድ ዓመት 700 መቶ ሺ ክፍያ በመፈፀም ሲያስቀር ፍቃዱ ዓለሙን ለሁለት ዓመት በ1 ሚሊየን 400 ሺ ወደ ደመወዝ ሲቀየር 63ሺ 636 ብር እና ኃይለየሱስ መልካንም ለአንድ ዓመት በ600መቶ 50 ሺ ብር የፊርማ ክፍያ ከቡድኑ ጋር እንዲቀጥሉ አድርጓል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ የአዲስ አበባ ከተማ እግር ኳስ ቡድን ለሙከራ ሁለት ተጨዋቾችን ከኬንያ በማስመጣት የሙከራ እድል ቢሰጥም ተጨዋቾቹ ከእኛ ሀገር ተጨዋቾች የተሻሉ ስላልሆኑ ወደ ሀገራቸው ተመልሰዋል፤ ክለቡ በቀጣይነት ከጋና እና ኬንያ ሌሎች ሁለት ተጨዋቾችን ለሙከራ ለማስመጣትም እየተዘጋጀ ይገኛል፡፡