የኢትዮጵያ ብ/ቡድን (ዋልያዎቹ) የዋና አሰልጣኝ ጉዳይ በጊዜ ይፋ አለመሆን ለተለያዩ አስተያየቶችና መላ ምቶች እየጋበዘ ነው ።የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ያወጣውን ባለ 7 ነጥብ የቅጥር ማስታወቂያ ተከትሎ ከ20 የበለጡ የሀገር ዉስጥና የባህር ማዶ አሰልጣኞች ያመለከቱ ቢሆንም ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ሰዓት ድረስ ማን ቀጣዩ የዋልያዎቹ አለቃ ይሆናል?ለሚለው ጥያቄ ምላሽ ማግኘት አልተቻለም።የተለያዩ የኤፍ ኤም የስፖርት ፕሮግራሞች የአዳማ ከተማው አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ለቦታው መመረጣቸውን የራሳቸውን የመረጃ ምንጭ ዋቢ በማድረግ ቢገልፁም ዘገባውን ከፌዴሬሽኑም ሆነ ምርጫውን ሲያከናውን ከቆየው የቴክኒክና ልማት ኮሚቴ ማረጋገጥ አልተቻለም። በዋልያዎቹ አሰልጣኝ ምርጫ ዙርያ የተፈጠረውን ዉዥንብር ተከትሎ ፌዴሬሽኑ ለሚዲያ አካላት በላከው መግለጫ “ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ለመቅጠር በወጣው ማስታወቂያ መሰረት በቴክኒክና ልማት ቃሚ ኮሚቴ ተዘጋጅቶ የቀረበው የዉሳኔ ሃሳብ በፌዴሬሽኑ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ዉሳኔ ያልተሰጠበትና ያልታየ መሆኑን እንገልፃለን”በማለት በኢሜል ያሳወቀ ሲሆን ነገ አሊያም ማክሰኞ በሚደረግ ስብሰባ የዋልያዎቹ አለቃ ማንነት በይፋ እንደሚታወቅ ነዉ የተሰማው።የቴክኒክና ልማት ኮሚቴው ባወጣው መመዘኛ መሠረት ምርጫውን አከናውኖ በነጥባቸዉ መሰረት ደረጃ ሰጥቶ በፖስታ በማሸግ ለሥራ አስፈፃሚው የመራው ሲሆን ሥራ አስፈፃሚው በቀረበለት መሰረት ምርጫውን ያፀድቀዋል ?ወይስ ውድቅ ያደርገዋል ?የሚለው ከወዲሁ የብዙዎችን ትኩረት የሳበ ሆናል።ፌዴሬሽኑ ባለው ሥልጣን መሠረት ምርጫውን የመሰረዝና በድጋሚ እንዲካሄድ የማድረግ ስልጣኑ እንዳለው ይታወቃል።ሰኞ ወይም ማክሰኞ ለዋልያዎቹ አለቃ ማንነት ቁርጥ ቀን።
አስተያየት ይስጡ