የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የዘጠነኛ ሳምንት ጨዋታ በዛሬው ዕለት መደረግ ሲጀምሩ ባህርዳር ከተማ ሲያሸንፍ ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ እንዲሁም ቦሌ ክፍለ ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ አቻ ተለያይተዋል።
ረፋድ 4:00 ጀምሮ በአበበ ቢቂላ ስታድየም በተደረገው ጨዋታ ባህርዳር ከተማ ሀምበርቾን 3 ለ 1 በሆነ ውጤት አሸንፏል።
በጨዋታው ሰላማዊት መንገሻ የባህርዳር ከተማን ሶስቱንም ግቦች በማስቆጠር ሶስታ ሰርታለች። ሰላማዊት በውድድር ዓመቱ ያስቆጠረቻቸውን የግብ ብዛቶችም አራት በማድረስ የኮከብ ግብ አግቢ መሪነቱን ተቀላቅላለች።
በተጨማሪም ሰላማዊት በውድድር ዓመቱ ሶስታ የሰራች የመጀመሪያዋ ተጫዋችም ሆናለች።
- ማሰታውቂያ -
ሀምበርቾን ከሽንፈት ያልታደገች ግብ ፍሬነሽ ዮሐንሽ ከመረብ አሳርፋለች።
የውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ተከታታይ ድል ያስመዘገበው ባህርዳር ከተማ ነጥቡን 13 በማድረስ ደረጃውን አሻሽሏል።
ሀምበርቾ በበኩሉ የውድድር ዓመቱን ስምንተኛ ሽንፈቱ ሆኖ ተመዝግቧል።
ቀትር 7:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ጋር አንድ ለአንድ በሆነ ውጤት ተለያይተዋል።
በጨዋታው ንጋት ጌታቸው ለሲዳማ ቡና ምርቃት ፈለቀ ደግሞ ለአርባምንጭ ከተማ ኳስና መረብን አገናኝተዋል።
ከመሪው ሀዋሳ ከተማ በአንድ ነጥብ ዝቅ ብሎ ያለው ሲዳማ ቡና አሸንፎ ወደ መሪነት መመለስ የሚችልበትን ዕድል ሳይጠቀም ቀርቷል።
በዕለቱ የመጨረሻ መርሐግብር ቦሌ ክፍለ ከተማን ከድሬዳዋ ከተማ አገናኝቶ ግብ ሳይቆጠርበት ተጠናቋል።
ውጤቱን ተከትሎ ነጥቡን 15 ያደረሰው ድሬዳዋ ከተማ በጨዋታው ሶስት ነጥቦችን ማሳካት ቢችል በደረጃ ሰንጠረዡ ከአናት መቀመጥ ይችል ነበር።
የሊጉ መርሐግብር በነገው ዕለትም ሲቀጥል ልደታ ክፍለ ከተማ ከአምናው ሻምፒዮን ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ረፋድ 4:00 ጀምሮ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።


