የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት መርሐግብር በዛሬው ዕለት በተደረጉ ሁለት ጨዋታዎች ጅማሮውን አድርጓል።
9:00 ላይ በጀመረው ቀዳሚው ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስሁል ሽረን ገጥሞ በፍፁም ጥላሁን ብቸኛ ግብ 1 – 0 አሸንፏል።
ያለፉትን ሁለት ዓመታት በባህርዳር ከተማ ያሳለፈው ፍፁም ጥላሁን በቡድኑ ቆይታው 50 የሊግ ጨዋታዎች አድርጎ 8 ግቦችን አስቆጥሯል።
በዚህ የውድድር ዘመን ግን በቅዱስ ጊዮርጊስ ማልያ ገና በ12ኛ ጨዋታው 5ኛ ግቡ ላይ ደርሷል።
- ማሰታውቂያ -
በተጨማሪም የውድድር ዘመን የቡድኑን ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነትን ከአማኑኤል ኤርቦ ጋር መጋራት ችሏል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ በውድድር ዘመኑ ካስቆጠራቸው 15 ግቦች 10 ወይም 66.7% በሁለቱ ተጫዋቾች የተገኙ ናቸው።
የዓመቱን ስድስተኛ ድል ያስመዘገበው ቅዱስ ጊዮርጊስ ነጥቡን 21 በማድረስ ከመሪው መቻል ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሶስት አጥብቧል።
ተሸናፊው ስሁል ሽረ ለአራተኛ ጊዜ ቅዱስ ጊዮርጊስን በገጠመበት ጨዋታ አሁንም ግብ የሚያስቆጥርለት ተጫዋች ማግኘት አልቻለም።
ከተከታታይ 12 ጨዋታዎች በአንዱ ብቻ ድል የቀናው ቡድኑ በ11 ነጥብ የ16ኛ ደረጃን ይዟል።
በቀጣይ ሳምንት በሚደረጉ ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ከድሬዳዋ ከተማ እንዲሁም ስሁል ሽረ ደግሞ ከአርባምንጭ ከተማ ይገናኛሉ።
በዕለቱ ሁለተኛ መርሐግብር አርባምንጭ ከተማ አዳማ ከተማን 2 – 0 ረቷል።
አህመድ ሁሴን በ13ኛው እንዲሁም በፍቅር ግዛው በ40ኛው ደቂቃ ላይ አዞዎቹን ባለ ድል ያደረጉ ግቦችን አስቆጥረዋል።
አርባምንጭ ከተማ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ድሉን ያስመዘገበም ሲሆን በአምስቱም ድል ባደረገባቸው ጨዋታዎች ላይ ግብ አላስተናገደም።
የአሸናፊነት ግቦቹ ለአህመድ ሁሴን የውድድር ዘመኑ ሶስተኛ ለበፍቅር ግዛው ደግሞ ሁለተኛ ግባቸው ነው።
በቀጣይ ሳምንት ጨዋታዎች አርባምንጭ ከተማ ከስሁል ሽረ ሲጫወት አዳማ ከተማ አራፊ ቡድን ነው።


