በስምንተኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ድል ሲመለስ ሁለት ቀይ የነበረው የመቻል እና ድሬዳዋ ጨዋታ እንዲሁም አስገራሚ ፉክክር የታየበት የነገሌ እና ሸገር መርሀግብር በአቻ ውጤት ተጠናቋል።
መቻል 1-1 ድሬዳዋ ከተማ
አዲስ አበባ ስታዲየም በብቸኝነት ዘጠኝ ሰዓት ሲል የጀመረው የመቻል እና ድሬዳዋ ጨዋታ ሁለት ቀይ ካርድ አስመልክቶን በአቻ ውጤት ተጠናቋል። መቻሎች አጀማመራቸው ጥሩ በማድረግ በቀጠሉበት ጨዋታ 30ኛው ደቂቃ ላይ አማካያቸውን ለማጣት ተገደዋል። መናፍ ኢሞሮ የድሬዳዋው አማካይ አቡበከር ሻሚል ላይ በሰራው አደገኛ ጥፋት የዕለቱ ዋና ዳኛ ሀይማኖት አዳነ በቀጥታ ቀይ ካርድ ካስወጡት በኋላ ባሉት ቀሪ ደቂቃዎች የቁጥር ብልጫውን ለመጠቀም ጥረት ያደረጉት ብርቱካናማዎቹ 36ኛው ደቂቃ አቡበከር ሻሚል በጥሩ ዕይታ ያቀበለውን ኳስ መሐመድ ኑርናስር ፍጥነቱን ተጠቅሞ ከመረብ በማሳረፍ የአሰልጣኝ ይታገሱ እንዳለን ቡድን መሪ አድርጓል።
በሁለተኛው አጋማሽ ጨዋታው ሲመለስ ከዕረፍት በፊት ለመቻሉ አማካይ በቀይ መውጣት ምክንያት የነቀረው አቡበከር ሻሚል በሁለት ቢጫ በሰራው ጥፋት 51ኛው ደቂቃ ላይ በቀይ ካርድ ከወጣ በኋላ መቻሎች ወደ ጨዋታ ለመመለስ በተለይ በዕለቱ ልዩነት ፈጣሪ በነበረው ጋናዊው አጥቂ ኮሊስ ኮፊ አማካኝነት በድግግሞሽ ማጥቃታቸውን በይበልጥ አሳድገዋል። ጎል አስቆጣሪያቸውን መሐመድ ኑርናስርን በጉዳት ለተጨማሪ ህክምና ወደ ሆስፒታል ሸኝተው በተጋጣሚያቸው በእንቅስቃሴ በቀጣዮቹ ደቂቃዎች የተበለጡት ድሬዳዋ ከተማዎች 63ኛው ደቂቃ ከኮሊስ ያገኘው ኳስ አብዱልከሪም ወርቁ ወደ ጎልነት ለውጦ ጨዋታው በመጨረሻም 1ለ1 ተቋጭቷል።
- ማሰታውቂያ -
ቅዱስ ጊዮርጊስ 1-0 አርባምንጭ ከተማ
በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ፈረሰኞቹን ከአዞዎቹ ያደረጉት መርሀግብር በቅዱስ ጊዮርጊስ የበላይነት ከድምዳሜ ደርሷል። ተመጣጣኝ የሚባል ነገር ግን ብዙም ሳይነቱ ጎልቶ ባልተስተዋለው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ መጠነኛ የማጥቃት ደመነብስን ተላብሰው ሲጫወቱ የተስተዋሉት ቅዱስ ጊዮርጊሶች 43ኛው ደቂቃ ላይ ጎል አስቆጥረዋል። ከግራ መስመር በኩል ተገኑ ተሾመ ወደ ውስጥ የላካት ኳስ ተጨራርፋ የደረሰችው ፀጋ ከድር ወደ ጎልነት ለውጧት ቡድኑ መሪ አድርጓቸዋል።
ከዕረፍት ተመልሶ በቀጠለው እና አዞዎቹ የተጫዋች ለውጥን ጭምር አድርገው መጫወት ቢችሉም ቅዱስ ጊዮርጊሶች በተለይ በቢኒያም ፍቅሬ እና ተገኑ ተሾመ አማካኝነት የሚያስቆጩ አጋጣሚዎችን ፈጥረው ይበልጥ የጎል መጠናቸውን ከፍ የሚያደርጉበትን ዕድሎች ቢያገኙም ጨዋታው በመጨረሻም በተቆረጠረችዋ ብቸኛ ጎል ፈረሰኞቹን ከተከታታይ ነጥብ መጣሎች በኋላ 1ለ0 አሸናፊ አድርጋ ተጠናቋል።
ነገሌ አርሲ 2-2 ሸገር ከተማ
እጅግ አስገራሚ የሜዳ ላይ ፉክክር እና የአራት ጎሎች ድራማን ያሳየን የምሽቱ የኦሮሚያ ደርቢ ጨዋታ በአቻ ውጤት ተቋጭቷል። በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ማኑሄ ወልደፃዲቅ እየተመራ አመሻሹን በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ሜዳ የተደረገው ጨዋታ በመጀመሪያው አርባ አምስት ከፉክክር አንፃር መጠነኛ መልክ ቢኖረውም በአንፃራዊነት ነገሌ አርሲዎች በፈጣን ሽግግር የተሻሉበት ሸገሮች በበኩላቸው ወጥ ባይሆነም በጥልቅ እንቅስቃሴ መጫወት መርጠው የተስተዋሉበት ነበር።
ከመጀመሪያው አጋማሽ ይልቅ ከፍተኛ መሻሻሎችን ይዞ የተመለሰው ከ አስደናቂ የሜዳ ላይ ግለቶችንም ያሳየን ሁለተኛው አጋማሽ ሸገር ከተማዎች አሳድገው የተመለሱን የመስመር አጨዋወት ጫና በሚፈጥር እንቅስቃሴ ተጋጣሚያቸው ላይ ጎል አስቆጥረዋል። 55ኛው ደቂቃ ላይ ናትናኤል ዘለቀ በአግባቡ ያቀበለው ኳስ ከሳጥኑ የግራ ክፍል ሆኖ ያገኘው ጀቤሳ ሜኤሳ የተከላካዮች ዝንጉነት ታክሎበት የቀድሞው ክለቡ ላይ ጎል አስቆጥሮ ቡድኑን መሪ ሲያደርግ ደስታውን ሳይገልፅ ቀርቷል። ጨዋታው ቀጥሎ 70ኛው ደቂቃ ላይ እንደደረሰ የአሚር አብዶ ጥሩ ዕይታ ታክሎ ጀቤሳ ሜኤሳ በድጋሚ ጎል በማስቆጠር ለራሱም ለቡድኑም ሁለተኛ ጎል አድርጓታል።
ሁለት ጎሎች ካስተናገዱ በኋላ የተጫዋቾችን ለውጥ በማድረግ ልማደኛውን የመስመር አጥቂ ከቤ ብዙነህን መነሻ የማጥቃት ምንጫቸው አድርገው የታዩት ነገሌዎች 75ኛው ደቂቃ ምስጋናው መላኩ አቀብሎት ግሩም ጎል ከቤ ብዙነህ ከመረብ አዋህዶ ቡድኑን ወደ ጨዋቻ ጨዋታ መልሷል። መደበኛው የጨዋታ ደቂቃ ተጠናቆ በጭማሪው ሰባት ደቂቃ ውስጥ ከሳጥኑ ጠርዝ 90+2 ላይ የተገኘን የቅጣት ምት ሮሆቦት ሰለሎ የባህሩ ነጋሽ የንቃት ጉድለት ታክሎበት በቀጥታ የመታት ኳስ ከመረብ አርፋ በመጨረሻም በበርካታ ደጋፊዎች ፊት የተደረገው ጨዋታ 2ለ2 ተፈፅሟል።



