በተመሳሳይ አንድ አንድ ጎል የተቆጠረባቸው ሦስት ጨዋታዎች በመሸናነፍ ተጠናቀዋል።
ምድረ ገነት ሽረ 1-0 ሀዋሳ ከተማ
ከቀትር መልስ የአዲስ አበባ ስታዲየም ያስተናገደው የምድረ ገነት ሽረ እና ሀዋሳ ከተማ ጨዋታው በሰሞነኛ አቋማቸው በተሻለ ቁመና ላይ በሚገኙት ሽረዎች አሸናፊነት ተጠናቋል። በመጀመሪያዎቹ አስራ አምስት ደቂቃዎች ተመጣጣኝ በሚመስለው የቡድኖቹ ጨዋታ 34ኛው ደቂቃ ተካልኝ ደጀኔ ያሻገራትን ኳስ የግብ ዘቡ ሰይድ ሀብታሙ በአግባቡ አለመቆጣጠሩን ተከትሎ ኳሷን ያገኘው አቤል ማሙሽ ወደ ጎልነት ለውጦ ቡድኑን ቀዳሚ አድርጓል።
የሀዋሳ ከተማ በእንቅስቃሴ መሻሻል ምድረ ገነት ሽረዎች ደግሞ ወደ ኋላ በማፈግፈግ ነጥብ ይዞ ለመውጣት ጥረት ያደረጉበት ሁለተኛው አጋማሽ ሀዋሳዎች ጎል አስቆጥረው አወዛጋቢ በሆነ የዳኛ ውሳኔ የተሻረበት እና መደበኛው የጨዋታ ደቂቃ ተጠናቆ የተሰጠው ጭማሪ ሳያልቅ የዕለቱ ዋና ዳኛ አሸብር ሰቦቃ ፊሽካቸውን ያሰሙበትን ውዝግቦችን ብናስተውል ጨዋታው በመጨረሻም በምድረ ገነት ሽረ 1ለ0 አሸናፊነት ተደምድሟል።
- ማሰታውቂያ -
ሲዳማ ቡና 1-0 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
የሲዳማ ቡና ፍፁማዊ የእንቅስቃሴም ሆነ የሙከራ የበላይነት ከፍ ብሎ በታየበት የመጀመሪያው አጋማሽ ጎል የተቆጠረው ገና በመጀመሪያው ደቂቃ ነበር። 4ኛው ደቂቃ ላይ ከሬድዋን ናስር የመጣለትን ኳስ ተከላካዩ ብርሀኑ በቀለ በግንባር ገጭቶ ፓላክ ቾል መረብ ላይ በማሳረፍ ቡናማዎቹን ቀዳሚ አድርጓቸዋል።
ከዕረፍት መልስ የተጫዋች ለውጥን በማድረግ የአሰልጣኝ በፀሎት ልዑልሰገዱ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ወደ ጨዋታ ለመመለስ ጥረት ባደረገበት እና ሲዳማ ቡናዎች በበኩላቸው ለኋላ ክፍላቸው መጠነኛ ጥንቃቄን በመውሰድ ማጥቃቱ ላይ ለተጨማሪ ጎል መጫወት የቻሉ ቢሆንም የዕለቱ ዳኛ ዳንኤል ይታገሱ ንግድ ባንኮች በሳይመን ፒተር አማካኝነት ጎል አስቆጥረው መስመር አላለፈች በሚል ከተሻረችዋ ክስተት በኋላ ጨዋታው ሲዳማ ቡናን 1ለ0 አሸናፊ አድርጎ ሲጠናቀቅ ቡድኑም ሊጉን መምራቱን አጠናክሮ ቀጥሏል
ኢትዮጵያ ቡና 1-0 ሀድያ ሆሳዕና
ቡናማዎቹ በሀያ ደቂቃዎች ውስጥ በይበልጥ ከመስመር መነሳትን መርጠው ለመጫወት በጣሩበት ወቅት 11ኛው ደቂቃ ላይ ጎል አስቆጥረዋል። ሚኪያስ በዳሶ ወደ ጎል የመታትን ኳስ የሀድያ የተከላካይ ስፍራ ተጫዋች ሳጥን ውስጥ ኳስን በእጅ በመንካቱ የተሰጠውን የፍፁም ቅጣት ምት ናይጄሪያዊው አጥቂ አቡበከር አዳሙ ወደ ጎልነት ለውጦ ቡድኑን መሪ እንዲሆን አስችሏል።
በሁለተኛው አጋማሽ የተጫዋች ለውጥን ከማድረጋቸው ባለፈ የአጥቂ ክፍላቸውን በማብዛት ወደ ጨዋታ ቅኝት በይበልጥ የገቡት እና በርካታ አጋጣሚዎችን የፈጠሩት ሀድያ ሆሳዕናዎች ቢሆንም የመጨረሻው ሜዳ ላይ ያሳዩ በነበሩት ደካማ የአፈፃፀም ጉድለት የተነሳ ከዕረፍት በፊት በተቆጠረባቸው ጎል ጨዋታው በኢትዮጵያ ቡና 1ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።


