በህዳሴ ዋንጫ የምድብ አንድ ሁለተኛ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፋሲል ከነማን 4 ለ 1 አሸንፏል።
ከቀን 10:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ ፍፁም ጥላሁን ፣ አቤል ያለው ፣ ቡአይ ኩዬት እና ተገኑ ተሾመ የቅዱስ ጊዮርጊስን ግቦች ሲያስቆጥሩ ቃልኪዳን ዘላለም የፋሲል ከነማን ብቸኛ ግብ ከመረብ አሳርፏል።
ከጨዋታዉ በኋላ የሁለቱም ቡድን አሰልጣኞች የድህረ ጨዋታ አስተያየት የሰጡ ሲሆን የፋሲል ከነማው ዋና አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ውድድሩ ተጫዋቾችን ለማየት ዕድል የሚሰጣቸው መሆኑን ተናግረዋል።
የመጀመሪያ ጨዋታቸው መሆኑን ያስታወሱት አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ያሉባቸውን ችግሮች እና ክፍተቶች ለማየት እንደሚረዳቸው ገልጸዋል።
- ማሰታውቂያ -

በተለያዩ አሰልጣኞች ከተነሳው የደመወዝ ጣሪያ የፋይናንስ ስርዓት መመሪያው ጋር በተያያዘም አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ተከታዩን ብለዋል።
“ይሄ አስትዳደራዊ ጉዳይ ነው። እኔ በሜዳ ላይ ነው መመለስ የምችለው ፤ የተስማሙት በአስተዳደር ላይ ያሉ ሰዎች ናቸው። እኛ አሰልጣኞች ተሰብስበን አይደለም። ስለዚህ ከአሰልጣኞች ጋር ምንም አይገናኝም። ግነ ባለው ሁኔታ ላይ የሚያምኑ ከሆነ ክለቦቹ ካመኑበት እኛ ሜዳ ላይ የሚሰራውን ስራ ነው ፌር ነው አይደለም አላውቅም እንግዲህ የወሰኑት ሰዎች መነጋገር ያለባቸው።”
የቅዱስ ጊዮርጊሱ ዋና አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ በበኩሉ ቡድኑ ሜዳ ላይ በነበረው እንቅስቃሴ ደስተኛ እንደነበር የተናገረ ሲሆን በዛሬው ጨዋታ ካለፈው ጨዋታ የተሻለ ነገር ስለመኖሩ ገልጿል።
“በሁለቱ ጨዋታ ሁለት ቡድን አዘጋጅተን ዓመቱን ሙሉ የምንጠቀምባቸውን ተጫዋቾች እዚህ ውድድር ላይ ማየት ነው የፈለግነው ፤ እሱ አንዱ ድላችን ነው ብለን እናስባለን።”
“ሁለተኛው በሁለቱ ቡድኖች መሀል የነበረው አንዱ ልዩነት ልምድ ነው። በዛሬው ቡድናችን ላይ ጨዋታውን መቆጣጠር የሚችሉ ከፊት በጣም ካገኙ ጎል ማግባት የሚችሉ አስፈሪ የአጥቂ ክፍል አለን። እሱ ትልቅ ልዩነት ነው ብለን እናስባለን። ለምን ? ባለፈው ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ ያገኘናቸውን የግብ ዕድሎች ብንጠቀም ምናልባት የበለጠ ጨዋታው ውስጥ እንሆን ነበር። ያ ነው ልዩነቱ ብዬ አስባለሁ።”
በአማካይ ክፍል ላይ እንደ በረከት ወልዴ እና አብርሃም ጌታቸው አይነት ተጫዋቾችን ያጣው ቅዱስ ጊዮርጊስ በወጣት እና ልምድ ያላቸው ተጫዋቾችን በማጣመር ጠንካራ የመሀል ክፍል ለመገንባት እየሰሩ መሆናቸውን አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ ተናግሯል።
በጨዋታው ኮከብ ሆኖ ስለተመረጠው ሀብታሙ ጉልላትም አሰልጣኝ ፋሲል ይህንን ብሏል።
“ሀብታሙ ሁለገብ የምትለው አይነት ተጫዋች ነው። የራስ መተማመኑን በደንብ ከፍ ሲያደርግ ከዚህ የተሻለ ተጫዋች መሆን ይችላል። በቴክኒክም ሆነ በአካል ብቃት ጥሩ የሆነ ተጫዋች ነው። አዕምሮው ላይ እንሰራለን በራሱ እንዲተማመን የተሻለ መጫወት ይችላል። ሌሎችም በታዎች ላይ ብናስገባው ጥሩ መጫወት ይችላል ብለን እናምናለን። ዛሬ ኮከብ መሆኑ የበለጠ ከፍ ያደርገዋል። ኃላፊነቶች ይመጣሉ እንደዚህ አይነት ነገሮች እንዲረዳ ከኋላ ሆነን እናስተምረዋለን።”
በዛሬው ጨዋታ ከረጅም ጊዜ በኋላ ዳግም በቅዱስ ጊዮርጊስ ማልያ የተጫወተው አቤል ያለው ቡድኑን በአምበልነት እየመራ በመግባት ግብም ማስቆጠር ችሏል።
አቤል ያለው ትልቅ አቅም ያለው ተጫዋች መሆኑን ያነሳው አሰልጣኝ ፋሲል በቡድኑ ላይ የፈጠረውን መነቃቃት እንዲህ ገልፆታል።
“አቤል ያለውን ከፊት ማሰለፍ ለቡድኑ ትልቅ አቅም ነው። ሌሎች ተጫዋቾች እሱን እንደ አርአያ ነው የሚወስዱት የቅዱስ ጊዮርጊስን ባህል ከመረዳት አንፃር የበለጠ ከመጫወቱም ጎል ከማግባቱም በላይ እንደ መሪ በብዙ ነገር ይረዳናል ብለን እናስባለን። ዛሬ ከረጅም ጊዜ በኋላ ነው የተጫወተው ባሳየው ፐርፎርማንስ ደስተኛ ነኝ። የፊት ነስ ደረጃው ከፍ ሲል ሁሉም ሰው የሚያውቀውን አቤል ሜዳ ላይ እንደምናየው እርግጠኛ ነኝ።”


