የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 10ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በሳምንቱ መጨረሻ የሚደረጉ ሲሆን ዛሬ (ቅዳሜ) ሶስት ጨዋታዎች የተደረጉ ሲሆን ነገ (እሁድ) ደግሞ ቀሪ አምስት ጨዋታዎች የሚደረጉ ይሆናል። በነገው እለት ከሚደረጉት ጨዋታዎች መካከል ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ ባህር ዳር ከተማ የሚያደርጉትን ጨዋታ ለእናንተ እንዲስማማ አድርገን እንደሚከተለው ዳሰነዋል። መልካም ንባብ።
ጨዋታ: ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ ባህር ዳር ከተማ
የጨዋታ ቀን: እሁድ ጥር 17/2012
የጨዋታ ሰዓት: 9:00
የጨዋታ አርቢትር: ኢንተርናሽናል አርቢትር በላይ ታደሰ
የጨዋታ ቦታ: አዲስ አበባ ስታዲየም
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 10ኛ ሳምንት ላይ የደረሰ ሲሆን በዚህ ሳምንትም በ9ኛው ሳምንት ወደ አብዮ ኤርሳሞ ስታዲየም ተጉዘው ከሀድያ ሆሳዕና ጋር አቻ የተለያዩት ቅዱስ ጊዮርጊሶች በሜዳቸው ባህር ዳር ከተማን ያስተናግዳሉ።
ሁለቱ ቡድኖች የየራሳቸው የሆነ የሜዳ ላይና ከሜዳ ውጪ የሚታዩ ችግሮች ያሉባቸው ናቸው። በቅዱስ ጊዮርጊስ በኩል አሁንም ከሜዳ ውጪ ጨዋታዎችን አለማሸነፍ እንደ ትልቅ ድክመት የሚቆጠር ሲሆን የሊጉ መሪ መሆን የሚችሉበትን እድል በተደጋጋሚ ጊዜ ሲያሳጣቸው ተስተውሏል። ይህንንም ተከትሎ ከክለቡ የበላይ አካላት ለአሰልጣኞቹ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጠ ይታወሳል። በባህር ዳር ከተማ በኩልም እንደ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሁሉ ከሜዳቸው ውጪ ማሸነፍ እንደተቸገሩ የሚታይ ሲሆን ከሜዳ ውጪ ደግሞ የተጫዋቾቹ የደሞዝ ክፍያ ጉዳይ አነጋጋሪ ሆኗል። ተጫዋቾቹ ከወልዋሎ ጨዋታ በፊት የ3 ወር ደሞዛቸው እንዳልተከፈላቸው እና ክፍያው ሳይፈፀም ጨዋታ እንደማይጫወቱ ልምምዳቸውንም እንደማይሰሩ ለክለቡ አሳውቀው የነበረ ሲሆን ሆኖም ግን ከክለቡ ጋር በተደረገ ድርድር የ1 ወር ደሞዝ ተከፍሏቸው የቀሪ ሁለት ወር ደሞዛቸው በሂደት እንደሚከፈላቸው ከስምምነት ላይ ደርሰው ነበር ወልዋሎ አ.ዩ.ን የገጠሙት። ይህ ችግር አሁንም እልባት ማግኘት ባለመቻሉ የባህር ዳር ከተማ ተጫዋቾች ወደ አዲስ አበባ መጓዝ ነገር አጠራጣሪ የነበረ ቢሆንም የቡድኑ አባላት ከትናንት በስቲያ ሀሙስ ከምሽቱ 2:00 ሲል አዲስ አበባ ገብተዋል።
በዘንድሮው የውድድር አመት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቀጥተኛ እና ፈጣን አጨዋወትን ሲጫወቱ ያስተዋልናቸው ሲሆን ለዚህ አጨዋወት ደግሞ ሀይደር ሸረፋ፣ አቤል ያለው እና ጋዲሳ መብራቴ ወሳኙን ድርሻ ይወስዳሉ። በፊት መስመር ደግሞ ግብ አዳኙ ጌታነህ ከበደ መኖሩ በ9 ጨዋታዎች 16 ግቦች ለተቆጠሩባቸው ባህር ዳር ከተማዎች ፈተና ይሆናል። ሌላው የግብ አዳኝ ሳላዲን ሰዒድ አለመኖር ለባህር ዳር ከተማዎች እፎይታ ነው።
በባህር ዳር ከተማ በኩል ቡድኑ ብዙ ግብ የሚቆጠርበት ቢሆንም የግብ ማግባት ችግርም የለበትም። ለዚህ እንደ ማሳያ ሊጠቀስ የሚችለው ባደረጓቸው 9ጨዋታዎች 16 ግቦችን ያስቆጠሩ ሲሆን ይህም በአማካይ በየጨዋታው 1.8 ግቦችን ያስቆጥራሉ ማለት ነው። ለዚህ ደሞ አማካዩ ፍፁም ዓለሙ፣ ማማዱ ሲዲቤ እና ግርማ ዲሳሳ እያሳዩ ያሉት ጥምረት ወሳኙን ሚና ይጫወታል። በሊጉ ትንሽ ግብ (6 ግቦች) የተቆጠሩባቸው ፈረሰኞቹ እና በሊጉ ከፋሲል ከነማ ቀጥሎ በርካታ ግቦችን (16 ግቦች) ያስቆጠሩት የጣና ሞገዶች የሚያደርጉት ጨዋታ በእግር ኳስ አፍቃሪው ዘንድ በጉጉት የሚጠበቅ ነው።
ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ ካደረጓቸው 9ጨዋታዎች በ3ጨዋታዎች አሸንፈው በ5ጨዋታዎች አቻ ወጥተው በ1ጨዋታ ብቻ በመሸነፍ የሊጉ አናት ላይ ከሚገኘው መቐለ 70 እ. በ5ነጥቦች ዝቅ ብሎ በ14ነጥቦች 5ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ሲችሉ ባህር ዳር ከተማዎች ደግሞ በ9ጨዋታዎች 4ጨዋታዎች አሸንፈው በ2ጨዋታዎች አቻ ተለያይተው በ4ጨዋታዎች ተሸንፈው ከተጋጣሚያቸው ቅዱስ ጊዮርጊስ እኩል 14ነጥቦችን ሰብስበው በ2ግብ ክፍያ ተበልጠው 6ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል።
እሁድ በአዲስ አበባ ስታዲየም 9:00 ሲል የሚጀምረው እና ኢንተርናሽናል አርቢትር በላይ ታደሰ በሚመሩት ጨዋታ ላይ በቅዱስ ጊዮርጊስ በኩል ሰልሀዲን ሰዒድ፣ ናትናኤል ዘለቀ እና ለዓለም ብርሀኑ የማይኖሩ ሲሆን በባህር ዳር ከተማ በኩል አቤል ውዱ እና ወሰኑ ዓሊ አሁንም ለጣናው ሞገዶች አገልግሎት የማይሰጡ ተጫዋቾች ናቸው።
አስተያየት ይስጡ