የይድነቃቸው ተሰማ የወጣቶች እግር ኳስ አካዳሚ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፣ የካፍ ፕሬዚዳንት ኢሳ ሃያቱ እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እና የስፖርት ሰዎች በተገኙበት ዛሬ ተመርቋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን መንግስት በስፖርቱ ዘርፍ ስኬት ለማስመዝገብ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፥ አካዳሚው አስተዋፅኦው የጎላ ይሆናል ብለዋል፡፡

የተለያዩ የስፖርት ማዘውተሪያዎች እና ስታዲየሞች በመንግስት እየተገነቡ ሲሆን፥ የግል ተቋማትም በስፖርቱ ዘርፍ አብረው መስራት ከፈለጉ በሩ ክፍት መሆኑን አንስተዋል አቶ ደመቀ፡፡
የካፍ ፕሬዚዳንት ኢሳ ሃያቱ በበኩላቸው፥ ኢትዮጵያ እግር ኳስን ለማስፋፋት በምታደርገው ጥረት የአካዳሚው መገንባት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት ነው የገለፁት፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ፥ አካዳሚውን ያስገነባው የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር በሀገሪቱ ላለፉት ዓመታት የእግር ኳስ አምባሳደር መሆኑን አንስተው፥ አካዳሚው ኢትዮጵያ በቀጣይ ክህሎት ያላቸው የእግርኳስ ተጫዋቾችን እንድታገኝ ያስችላታል ብለዋል፡፡
በቀጣይ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት በትኩረት እንሰራለን ያሉት ደግሞ የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ አብነት ገብረ መስቀል ናቸው፡፡
በሀገሪቱ ፈር ቀዳጅ የሆነውን የይድነቃቸው ተሰማ የወጣቶች እግር ኳስ አካዳሚ የሚጠበቅበትን አገልግሎት እንዲሰጥ በቅርስነት ሊጠበቅ እንደሚገባውም ነው አቶ አብነት ያሳሰቡት፡፡
ዛሬ የተመረቀው የይድነቃቸው ተሰማ የወጣቶች የስፖርት አካዳሚ በ70 ሚሊየን ብር ወጪ የተገነባ ሲሆን፥ ሁለት እግር ኳስ ሜዳዎችና ጅምናዚየምን አካቶ የተሰራ ነው፡፡
በ24 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ ያረፈው ይህ አካዳሚ፥ በአውሮፓ በእግር ኳስ አካዳሚ ስኬታማ በሆነቺው የሆላንድ ባለሙያዎች የሚተዳደር ይሆናል፡፡
በውስጡም የእንግዳ መቀበያ፣ የጤና ማዕከላት፣ እና የመመገቢያ ኣዳራሽ ተሰርቶለታል፡፡
አካዳሚው ሙሉ በሙሉ ስራ ሲጀምርም በአንድ ጊዜ ብቻ ከ80 እስከ 100 የሚሆኑ ወጣቶችን ማስተናገድ ይችላል፡፡
አካዳሚው ራሱን እስከሚችል ድረስም ሞሃ፣ ደርባ እና ሆራይዘን ፕላንቴሽን በጋራ 50 በመቶውን እንዲሁም ቢ ጂ አይ
ኢትዮጵያ 50 በመቶ ወጭውን በመሸፈን ድጋፍ ያደርጉለታል ተብሏል፡፡
አካዳሚው ሥራውን ሲጀምርም በየዓመቱ 10 ሚሊየን ብር ያስፈልገዋል ነው የተባለው፡፡
አስተያየት ይስጡ