[EXCLUSIVELY ]
አስራት ሀይሌ እና ደደቢት አልተለያዩም
ዛሬ በተለያዩ የማህበረሰብ ገፆች እና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች ላይ “አስራት ሀይሌ እና ደደቢት ተለያዩ” በሚል የተሰራጨው ዜና መሰረተ ቢስ መሆኑን ሁለቱም ወገኖች በተለይ ለሀትሪክ ስፖርት ድረ-ገፅ በሰጡት አስተያየት ገለፁ።
ስለ ሁኔታው ከድረ-ገፃችን የተጠየቁት አንጋፋው አሰልጣኝ አስራት ሀይሌ “የተወራው ወሬ ፍፁም ሀሰት ነው፤ ሚዲያው ከየት አምጥቶ እንዳወራው የማውቀው ነገር የለም። እኔና ደደቢት አልተለያየንም። እርግጥ ነው የጆሮ ህመም አጋጥሞኛል። ህመሙ ከጀመረኝ ቢቆይም ችላ ብዬው ቆይቻለሁ። ችግሩ ሲበዛብኝ ወደ ታዋቂው ከአንገት በላይ ስፔሻሊስት ዶ/ር ነጋ ጋር ሄጄ ብትዘገይም ደርሰህበታል። ከዚህ ትንሽ ብትቆይ ለቀዶ ጥገና ትዳረግ ነበር በማለት ጠዋትና ማታ የምወስደው ሶስት አይነት መድሀኒት እና የእረፍት ፈቃድ ሰጥተውኛል። የጆሮዬ በሽታ ያዞረኛል፣ ሚዛን ያሳጣኛል፣ ያቅለሽለሸኛል። በመሆኑም ሀኪም ባዘዘልኝ መሰረት እረፍት ላይ ነኝ። ቡድኑን ሜዳ ገብቼ ባልመራም ለአሰልጣኞቹ መመሪያ እሰጣለሁ፤ መልበሻ ክፍል ገብቼ እመክራለሁ። ደደቢቶች ክለቡ ካልፈረሰ አንለያይም ሲሉ ሞራሌን ገንብተውልኛል። ደመወዜ፣ ጥቅማ ጥቅሜ እና መኪና ሁሉ አልተቋረጠብኝም፤ ለዚህም አመሰግናቸዋለሁ” ብሏል።

– የክለቡ ስራ አስኪያጅ አቶ ሚኬኤሌ አምደመስቀል በበኩላቸው “ወሬው ውሸት ነው፤ እኛ እና አስራት አንለያይም፤ እርሱ ትልቅ ስም ያለው ሰው ነው፤ ስሙ ብቻ ይበቃናል። ከጤና ችግር ጋር በተያያዘ እረፍት ላይ ቢሆንም አሁንም ቡድኑን በልምምድ ሜዳ ላይ እያሰራ ይገኛል፤ ይህንን ማረጋገጥ የሚፈልግ ሚዲያ ካለ ነገ መጥቶ ልምምድ ሜዳ ላይ መመልከት ይችላል” በማለት ከአስራት ሀይሌ ጋር ተለያዩ የሚለው የሚዲያዎች ወሬ ውሸት መሆኑን ለሀትሪክ ስፖርት ድረ-ገፅ ገልፀዋል።
በምስጋናው ታደሰ እና በሙሴ ግርማይ የቀረበ
አስተያየት ይስጡ