በፕሪምየር ሊጉ የመጀመሪያው አመት ቆይታው ክስተት የሆነውን ቡድን ያሳየን አሰልጣኝ ቱሉ ደስታ (በረከት) ማነው ?
ተወልዶ ያደገው አዳሚ ቱሉ በምትባል ከዝዋይ (ባቱ ከተማ) ሰባት ኪሎ ሜትሮችን ብቻ ርቃ በምትገኘው ትንሽዬ ከተማ ውስጥ ነው። በትልቅ ደረጃ እግር ኳስን የመጫወት በለስ ባይቀናውም በትውልድ አካባቢው በሰፈር እና በትምህርት ቤት ውድድሮች ላይ ግን በመጫወት የልጅነት ጊዜውን አጣጥሞ አሳልፏል። በይበልጥ ለስልጠና ተሰጦ እንዳለው ገና በወጣትነት ዕድሜው በጊዜ መግባት የቻለው ጭምቱ ሰው ከሰፈር የጀመረው የማሰልጠን መንገድ ዝዋይ ላይ በአንድ ወቅት አነጋጋሪ የነበረውን ሼር ኢትዮጵያን ከአስር አመት በፊት ይዞ በማሰልጠን የክለብ ህይወትን በመቀላቀል ራሱን ከፍ ባለ የአሰልጣኝነት መንበር ላይ እንዲያስቀምጥ ሆነ ከዝዋይ (ባቱ ከተማ) መነሻቸውን የሚያደርጉ እግር ኳስ ተጫዋቾች በዕርሱ የስልጠና መንገድ እያለፉ ስማቸውን በጉልህ ማፃፍ ሲችሉ ብዙም ስሙ ሲነሳ የማይሰማ የነበረው ወጣቱ አሰልጣኝ ረጅም አመታትን ካሳለፈበት እና ራሱንም በደንብ ካበቃበት ባቱ ከተማ ክለብ የአሰልጣኝ በሽር አብደላን ወደ ሸገር ከተማ ማምራትን ተከትሎ በ2017 የውድድር ዘመን ነገሌን አርሲን በከፍተኛ ሊጉ በመረከብ ራሱን ለብዙሀኑ ከወርሀ መስከረም ጀምሮ መግለጥ ጀመረ።
በባቱ የአሰልጣኝነት ቆይታውን መረጃ ፍለጋን በምደውልባቸው ጊዜያቶች ሁሉ በዜናዎች ውስጥ ስሙ እንዲነሳ የማይፈልገው ቱሉ ደስታ አብዛኞቹ በረከት እያሉ መጥራት የሚቀላቸው ወጣቱ አሰልጣኝ እነሆ ጊዜው ደረሰ እና ነገሌ አርሲን በያዘበት አመት በከፍተኛ ሊጉ ደምቆ ምድቡን በበላይነት አጠናቆ ወደ ሀገሪቱ ትልቁ ሊጉ ከማሳደግ በዘለለ በአሸናፊ አሸናፊዎች ዋንጫ ሸገርን በመርታት በሁለት ዋንጫዎች ከነገሌ ጎን ለጎን ቱሉ የሚለውን ስምንም እንካቹ ለማለት በቅቷል።
ነገሌ አርሲን ባደገበት የመጀመሪያው አመት ወጣት ተጫዋቾችን ልምድ ካላቸው ጋር በማጣመር በሊጉ ክስተት የሆነ ቡድንን ማሳየት የቻለው የሊጉ አዲሱ ሰው ነገሌ ካደረጋቸው አስራ አራት ጨዋታዎች ሰባት አሸንፎ ፣ አራት አቻ ወጥቶ ሦስት ብቻ ሽንፈት ገጥሞት ፤ አስራ ስድስት ጎል አግብቶ ፣ ዘጠኝ ገብቶበት ፣ ሰባት ንፁህ ጎሎችን በመያዝ 25 ነጥቦችን ይዞ ከመሪው ሲዳማ ቡና በሦስት ነጥብ ዝቅ ብሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ መቀመጥም ሲችል የዚህ ክስተት ሰው አበርክቶ ቀላል የሚባል አይደለም።
- ማሰታውቂያ -
እንደ ከቤ ብዙነህ ፣ አለኝታ ማርቆስ ፣ ገብረመስቀል ዱባለ ፣ ምስጋናው መላኩ ፣ ቦና ቦካ ፣ ርሆቦት ሰለሎ ፣ ዘሩባቤል ሞላ እና ሌሎች አዳዲስ ፊቶችን ለሊጉ ያስተዋወቀን አሰልጣኙ ልምድ ካላቸው ዳዊት ተፈራ ፣ ሀቢብ ከማል እና በረከት ወልዴን ከመሰሉ ተጫዋቾች ጋር አዋህዶ ከፍ ባለ የማጥቃት ደመ ነብስ ለቡድኖች ስጋት የሆነ አቀራረብን በመገንባት ያ ጭምቱ ስሙም እንዲጠራ የማይፈልግ የነበረው አሰልጣኝ ዛሬ ግን ጊዜው ደርሶ በስራው እነሆ ስሜ ብሎ አስተዋውቆናል።


