በአዲስ አበባ እና አዳማ በተደረጉ ሦስት ጨዋታዎች ሽመልስ በቀለ ባስቆጠራት ብቸኛ ጎል ሐይቆቹ ድል ሲቀናቸው ድሬዳዋ ከ ኤሌክትሪክ ፣ መቐለ ከ ሸገር በተመሳሳይ ያለ ጎል ተፈፅመዋል።
ድሬዳዋ ከተማን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ያገናኘው የአዲስ አበባ ስታዲየም ቀዳሚው ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሁለተኛው አጋማሽ ደግሞ ተመጣጣኝ እንቅስቃሴዎችን ያየንበት ቢሆንም በሙሉ የጨዋታ ደቂቃው ልዩነት ፈጣሪ የጠሩ ዕድሎች ሳይፈጠሩበት ያለ ጎል ተጠናቋል።
በሊጉ ዘለግ ያለ የግኑኝነት ታሪክ ያላቸውን ሀዋሳ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስን ያገናኘው የአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲው መርሀግብር በመጀመሪያው አጋማሽ ደካማ እንቅስቃሴ እና አንድም ዒላማውን መጠበቅ ያልቻለ ሙከራዎችን ያስተዋልንበት ሆኖ ተገባዷል። ከዕረፍት መልስ ጨዋታ ሲቀጥል ገና ሰላሳ ሰከንዶች ብቻ እንደተቆጠሩ ሀዋሳ ከተማዎች ጎል አስቆጥረዋል። በጥሩ ንክኪ ወደ ግራ የደረሰውን ኳስ ፍቃደስላሴ ወደ ውስጥ ሲያሻግር ሀብታሙ ጉልላት በግንባር ሲያወጣው የሀዋሳው አማካይ ናትናኤል ሸጋሞ በግንባር አመቻችቶ የሰጠውን ሽመልስ በቀለ ልምዱን ተጠቅሞ ኬኒያዊው የግብ ዘብ ሻኪሉ ፋሩክ መረብ ላይ በማስቆጠር ሐይቆቹን መሪ አድርጓቸዋል።
ጎል ካስተናገዱ በኋላ ወደ ጨዋታ ቅኝት የገቡት ቅዱስ ጊዮርጊሶች በድግግሞሽ የሀዋሳ የመጨረሻው ሜዳ ላይ መድረስ ቢችሉም በጥራት የታጀቡ ሙከራን ማድረግ የቻሉት ግን በአንድ አጋጣሚ ነበር። ሀብታሙ ጉልላት ያሻማውን ኳስ ግብ ጠባቂው ሰይድ ነክቷት የተመለሰች ኳስን ተገኑ ተሾመ ግልፅ አጋጣሚን አግኝቶ ወደ ውጪ ከሰደዳት በኋላ በቀሪዎቹ ደቂቃዎች ጎሎችን ሳንመለከት ሽመልስ በቀለ የቀድሞው ክለቡ ላይ ባስቆጠራት ብቸኛ ጎል 1ለ0 ሀዋሳ አሸናፊ ሆነውበታል።
- ማሰታውቂያ -
የዕለቱ የማሳረጊያ በሆነው የአዳማ ጨዋታ መቐለ 70 እንርደርታን ከሸገር ከተማ ቢያገናኝም መቐለ በኳስ ቁጥጥሩ ሸገሮች በተወሰነ መልኩ በሽግግር ለመጫወት ጥረት ያደረጉ ቢመስሉም በመቐለ በኩል ፍፁም አለሙ ካደረጋቸው ሁለት ዕድሎች ውጪ በጎል ሳይታጀብ 0ለ0 ተፈፅሟል።


