የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ክለብ ካጋጠመው ውስጣዊ ችግር በዘላቂነት ለመፍታት የተቋቋመው የሽግግር ኮሚቴ ዛሬ ባደረገው ስብሰባ የኮሚቴውን ሰብሳቢ እና ምክትል ሰብሳቢ መርጧል።
በዚህም መሰረት አቶ ዮሐንስ ገረመው የሽግግር ኮሚቴው ሰብሳቢ ሆነው ሲመረጡ፣ አቶ አበባው ዘውዴ ደግሞ በምክትል ሰብሳቢነት እንዲሰሩ በሙሉ ድምፅ ተሰይመዋል።
ይህ የሽግግር ኮሚቴ የተመረጠው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን መተዳደሪያ ደንብ አንቀፅ 66 ቁጥር 1 መሰረት ሲሆን፣ ደንቡ ፌዴሬሽኑ በአጋርነት በሚሰሩ ወገኖች መካከል የሚፈጠሩ ውስጣዊ እና ሀገራዊ አለመግባባቶችን የመዳኘት ስልጣን እንዳለው ይደነግጋል።
ኮሚቴው በቀጣይ የክለቡን ሀብት እንዲያፈላልግ፣ የእለት ተእለት የክለቡን ስራ እንዲያከናውን፣ የክለቡን አዲስ መተዳደሪያ ደንብ እንዲያዘጋጅ፣ የስፖርት ማህበሩ አሁን ካለበት ሰው ስራሽ ችግር በማውጣት ጠቅላላ ጉባኤ እንዲካሄድ አስቻይ ሁኔታዎችን አመቻችቶ እንዲጠራ እና ክለቡን ወደ ታላቅነቱ እንዲያሸጋግር ሀላፊነት ተሰጥቶታል።
በስብሰባው ላይ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ድኤታ ክቡር መክዩ መሐመድ፣ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት አቶ ኢሳያስ ጅራ፣ የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ሃላፊ አቶ አሰግደው ሃይለጊዮርጊስ የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ የስፖርት ዘርፍ ም/ቢሮ ሀላፊ አቶ ዳዊት ትርፉ እና የአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት ኢ/ር ሃይለእየሱስ ፍስሃ በተገኙበት የተከናወነ ሲሆን አመራሮቹም ለኮሚቴው ድጋፋቸው እንደማይለይ አስታውቀዋል።
በመጨረሻም የሽግግር ኮሚቴው የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ክለብን ወደነበረበት ከፍታ እና ሀያልነት ለመመለስ በሚደረገው ጥረት የክለቡ ደጋፊዎች፣ አድናቂዎች፣ የእግር ኳስ አፍቃሪያን እና የክለቡ ጉዳይ ያገባናል የሚሉ አካላት ሁሉ አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ ከጎናቸው እንዲቆሙ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
አስተያየት ይስጡ