ዘንድሮ 90ኛ አመቱን እያከበረ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር ስምምነት የፈጸመው ሀይል ሰጪ እና በማዕድን የበለጸገ መጠጥ አቅራቢ ከሆነው ላይት ኢንቨስትመንት ኃ/የተ/የግ/ማህበር ጋር ነው።
ዛሬ በቢሾፍቱ ይድነቃቸው ተሰማ ስፖርት አካዳሚ በተፈጸመው ስምምነት መሰረት ላይት ኢንቨስትመንት ኃ/የተ/የግ/ማህበር ለቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር ለቀጣይ አንድ ዓመት የኤሌክትሮ ላይት ምርቶቹን ያቀርባል።ማህበሩ ደግሞ በፈንታው ተቋሙን በተለያዩ አማራጮች ያስተዋውቃል።
በስምምነቱ ስነስርአት ላይ የክለቡ ዋና ስራ አስኪያጅ ፍጹም ካሳዬ (ዶክተር) እና የላይት ኢንቨስትመንት መስራች ብሌን ታደሰ ስምምነቱን ፈጽመዋል። በስምምነቱ ላይ የታደሙት የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር የስነ-ምግብ ባለሙያ ሐዊ ተስፋዬ እንዳሉት ከሆነ ከዚህ ቀደም ለስፖርተኞች ኃይል ለመጨመርና ፈሳሽን ለመተካት ማር እና ስኳር በውሀ እየበጠበጡ በመስጠት ይጠቀሙ እንደነበር አስታውሰው ዛሬ ወደ ስፖርት ማህበሩ የመጣው ተቋም በዚህ ረገድ የላቀ ጠቀሜታ ያላቸውን ግብአቶች አቅርቦልናል። በዚህም ውጤታ ሆነናል ብለዋል።
የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር ምክትል አሰልጣኝ አዳነ ግርማ በበኩሉ ኤሌክትሮ ላይት ሀይል ሰጪ መጠጥን ላለፉት ሶስት ወራት በቡድኑ ውስጥ መጠቀማቸውንና ተጨዋቾችም ከዚህ ቀደም ከነበራቸው ብቃት በተጨማሪም ለውጦችን እንዳገኙበትና በዚህም ተጨዋቾችም ሆኑ የቡድኑ አባላት ደስተኛ መሆናቸውን ተናግሯል። ብሌን ታደሰ የላይት ኢንቨስትመንት ኃ.የተ.የግ.ማህበር መስራች እንዳሉትም በብዙ ልምዶችና ሳይንሳዊ ጥምረቶች በሀገራችን ለስፖርተኞች ተጨማሪ ሀይል የሚሰጠውና የወጣውን ፈሳሽ የሚተካውን ኤሌክትሮ ላይት ይዘው በመምጣት ከቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር ጋር ውል ማሰራቸው እንዳስደሰታቸውና ሌሎች የሊጉ ተወዳዳሪ ክለቦችና ሌሎች ስፖርተኞችም ሊጠቀሙበት ይገባል ብለዋል።
- ማሰታውቂያ -
ኤሌክትሮ ላይት እንዳለው የተነገረውና ሀይል ከመስጠት እና ፈሳሽን ከመተካት ባሻገር በውስጡ በያዛቸው የተለያዩ ማዕድናት ዘርፈ ብዙ ጥቅሞችን ያስገኛሉ ያሉት ደግሞ የላይት ኢንቨስትመንት የስነ-ምግብ አማካሪ የሆኑት አቶ አልአዛር ኪሩቤል
ናቸው።
የላይት ኢንቨስትመንት ኃ.የተ.የግ.ማህበር የሚያመርተው የኋይል ሰጪ ኤሌክትሮ ላይት በውስጡ የቫይታሚን ሲ፣ ቫይታሚን ቢ እንዲሁም ግሉኮስን እና ፖታሺየምን የያዘ ሲሆን ከስፖርተኞች በተጨማሪም ማንኛውም ሰው በውሐ በጥብጦ የሚጠጣው ሃይል ሰጪ መጠጥ ነው።ይህም በሚመለከተው የመንግሥት ተቋም የተረጋገጠ ነው ተብሏል። የላይት ኢንቨስትመንት ኃ.የተ.የግ.ማህበር ከአጋር ድርጅቶቹ ሂልቦተም መዝናኛ ማዕከል፣ከሂልቦተም ሬስቶራንትና ቡና ጋር በመተባበር የሚሰራ ሲሆን ከተመሰረተ ሶስት አመታትን ሲያስቆጥር በ2017 ዓ.ም የኤሌክትሮ ላይትን ይዞ ወደ ገበያው ተቀላቅሏል።


