ባህርዳር ከተማ እና ምድረ ገነት ሽረ ነጥብ ተጋርተዋል
የሲቢኢ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ10ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት መደረግ ሲጀምሩ አዲስ አበባ ስታድየም ላይ የተደረገው የባህርዳር ከተማ እና ምድረ ገነት ሽረ ጨዋታ 0 ለ 0 ተጠናቋል።
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ ባህርዳር ከተማዎች የተሻለ በመንቀሳቀስ በኳስ ቁጥጥር እና ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል በመድረስ ረገድ ከምድረ ገነት ሽረ የተሻለ ጊዜን አሳልፈዋል።
ደጋግመው የምድረ ገነት ሽረን የኋላ ክፍል የፈተኑት የጣና ሞገዶቹ የጠራ የግብ ዕድል ለመፍጠር ግን ደቂቃዎችን መታገስ የግድ ብሏቸው ነበር።
- ማሰታውቂያ -
በ24ኛው ደቂቃ ላይ ወንድወሰን በለጠ ከአማኑኤል ገብረሚካኤል የደረሰውን ኳስ ወደ ምድረ ገነት ሽረ ሳጥን ይዞ ገብቶ ለማስቆጠር ቢጥርም በአዲስ ተስፋዬ ጫና እና በሪችሞንድ አይ ጥረት ሳይቆጠር ቀርቷል።
መደበኛው የመጀመሪያ አጋማሽ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በተጨማሪ ደቂቃዎች ላይ ሔኖክ ይበልጣል ከቅጣት ምት የተነሳን ኳስ አግኝቶ ወደ ግብ ያደረገውን ጠንካራ ሙከራ ሪችሞንድ አይ አውጥቶታል።
በምድረ ገነት ሽረ በኩል ወደ ሳጥን በሚላኩ ኳሶች የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ቢጥሩም ፔፔ ሰይዶን የፈተነ ሙከራ ሳያደርጉ የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቋል።
በሁለተኛው አጋማሽ 66ኛ ደቂቃ ላይ ባህርዳር ከተማዎች መሪ መሆን የሚችሉበትን ዕድል አግኝተው ነበር።
አማኑኤል ገብረሚካኤል ወደ ግብ ያደረገውን ሙከራ ስንታየሁ ወለጪ በዕጁ መመለሱን ተከትሎ የተሰጠውን የፍፁም ቅጣት ምት መሳይ አገኘሁ ቢመታውም ሪችሞን አይ አድኖታል።
ተደጋጋሚ ጫና ማሳደራቸውን የቀጠሉት ባህርዳር ከተማዎች በ74ኛው ፣ 76ኛው እና 92ኛው ደቂቃዎች ላይ ወደ ግብ የቀረቡባቸውን ሙከራዎች ማድረግ ቢችሉም ኳስ እና መረብን ግን ለማነገናኘት አልቻሉም።
የባህር ዳር ከተማ ዋና አሰልጣኝ ደግአረግ ይግዛው ከጨዋታው በኋላ በሰጡት አስተያየት እንደነበረን ብልጫ አሸንፈን መውጣት ይገባን ነበር ሲሉ ተናግረዋል።
ቡድናቸው ለማሸነፍ የነበረውን ጥረት ያደነቁት አሰልጣኙ ነገር ግን ያ ጥረት በቂ አለመሆኑ ሶስት ነጥብ ይዘው እንዳይወጡ እንዳደረጋቸው ገልጸዋል።
አሁን ላይ ግብ ጠባቂ የቡድን 75 በመቶ ነው ያሉት የምድረ ገነት ሽረው አሰልጣኝ ዳንኤል ፀሐዬ በበኩላቸው የሪችሞንድ አዬ ብቃት በጨዋታው አስደናቂ እንደነበር ጠቅሰዋል።
ኳሶችን ከመሀል ሜዳ ተጫዋቾች ወደ መስመር ተጫዋቾች በማድረስ ለማጥቃት አቅደው ስለመግባታቸው የተናገሩት አሰልጣኙ ነገር ግን መረጋጋት አለመኖሩ ቡድናቸው ያሰበውን አሳክቶ እንዳይወጣ እንዳደረገው ተናግረዋል።
በ11ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ምድረ ገነት ሽረ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ እንዲሁም ባህርዳር ከተማ ከፋሲል ከነማ ይጫወታሉ።


