“ህዳሴ ዋንጫ” በሚል ስያሜ የሚደረገው 19ኛው የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ በዛሬው ዕለት በይፋ ተጀምሯል።
በአዲስ አበባ ስታድየም በተደረገው የመክፈቻ ጨዋታ መቻል በሁለተኛው አጋማሽ ባስቆጠራቸው ግቦች ቅዱስ ጊዮርጊስን 4 ለ 0 አሸንፏል።
ከጨዋታዉ በኋላ ከሀትሪክ ስፖርት ድህረ ገፅ ጋር ቆይታን ያደረገው የቅዱስ ጊዮርጊሱ ዋና አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ ስለ ጨዋታው ተከታዩን ብሏል።
“ጨዋታው ሁለት አይነት መልክ አለው ፤ የመጀመሪያ አጋማሽ በጣም ጥሩ የሚባል ነው። በሁለተኛው አጋማሽ ደግሞ ጎሎቹ ቶሎ ቶሎ መቆጠራቸው ተጫዋቾቻችንን ጫና ውስጥ ከቷቸዋል። እንደምታየው ወጣቶች ስለሆኑ በቀላሉ መመለስ አልቻሉም።በኋላ ደግሞ በቀይ ካርድም ወጣብን ፤ እነዛ ጨዋታውን ለውጠውታል ብዬ አስባለሁ።”
- ማሰታውቂያ -
“ግን በመጀመሪያው አጋማሽ ጨዋታውን በበለጥንበት ሰዓት ጎሎች ብናገባ የተለየ ይሆን ነበር። እኛ ልምምድ ከጀመርን አስር ቀናችን ነው። ስለዚህ አዳዲስ ተጫዋቾቻን ወጣቶቹን የት እንዳሉ ያየንበት ነው። በሁለተኛው አጋማሽ የአካል ብቃት ደረጃችን ሊወርድ እንደሚችል የሚጠበቅ ነው።”
የመጀመሪያው አጋማሽን የቡድኑ እንቅስቃሴ ጥሩ መሆኑን የጠቀሰው አሰልጣኝ ፋሲል አንዳንድ አዳዲስ ተጫዋቾች ከጠበቀው በላይ እንዳገኛቸው ተናግሯል።
አክሎም ወደዚህ ወድድር የመጣነው ዘግይተን ንግግር እንደመጀመራችን የተጫዋቾቻችን የአካል ብቃት እና የጨዋታ ዝግጁነት ከፍ ለማድረግ ነው ተጫዋቾቻችን በሚገባ አይተናል ብሏል።
በጨዋታው በሰፊ ውጤት መሸነፋቸው በቡድኑ ላይ የሚፈጥረው የስነ ልቦና ጫና ይኖር ይሆን ተብሎ ለቀረበለት ጥያቄም ይህን ብሏል።
“በዚህ ማልያ መሸነፍ አይዋጥም። ግን ስንመጣ ይህን ተነጋግረን ነው የመጣነው ካለንበት ደረጃ እና ከሸፈነው የልምምድ ጊዜ አንፃር መጥፎ ነገር እንኳን ቢያጋጥመንም በአዕምሮ ደረጃ ጠንክረን ወደሚቀጥለው ጊዜ እንደምንሻገር እርግጠኛ ነን።”
በጨዋታው በቡድኑ በኩል ያሉት የፊት መስመር ተጫዋቾች አቤል ያለው እና ቢንያም ፍቅሬ በጨዋታው መሰለፍ ያልቻሉት መጠነኛ ጉዳት ስላገጠማቸው አለመጫወታቸውን ተናግሯል።
አክሎም በቀጣይ ሀሙስ ከፋሲል ከነማ በሚያደርጉት ሁለተኛ ጨዋታ የመሰለፋቸው ነገር በማገገም ሁኔታቸው ላይ እንደሚወሰን ተናግሯል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ በቀጣይ ሌሎች ተጫዋቾችን ወደ ክለቡ ተጨማሪ ተጫዋቾች ያስፈርም እንደሆነ ላቀረብንለት ጥያቄ ተከታዩን ብሏል።
“አንድ ግብ ጠባቂ እናመጣለን ብለን እናስባለን። ምናልባት ክፍት ቦታዎቻትን ላይ የምንጨምራቸው ተጫዋቾች ሊኖሩ ይችላሉ።”
በአዲስ አበባ ስታድየም ላይ በደጋፊዎቻችን ፊት በመጫወታችን ደስ ብሎናል ያለው አሰልጣኝ ፋሲል ቀጣይ የሊጉንም ጨዋታዎች እዚህ ሜዳ ስለምናደርግ ተጫዋቾንንም በዚህ ሜዳ ላይ ማየታችን ደስ ብሎናል ሲል ተናግሯል።
ይህ የቅድመ ውድድር ዘመን ዝግጅቱ አካል ነው ፤ የተጫዋቾቻችንን አቅም በአዕምሮም በአካልም ለማዘጋጀት እየሰራን ነው ሲልም አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ ገልጿል።


