በ19ኛው የአዲስ አበባ ከተማ የህዳሴ ዋንጫ የምድብ የመጨረሻ ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት ተደርገዋል።
ቀዳሚው ጨዋታ ከ8:00 ጀምሮ በምድብ አንድ በሚገኙት መቻል እና ፋሲል ከነማ መካከል ተደርጎ መቻል 3 ለ 1 አሸንፏል።
ከጨዋታዉ በኋላ በነበረው የድህረ ጨዋታ ቆይታ የመቻል ዋና አሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረት በቀዳሚው ጨዋታ የነበረውን የቡድኑን እንቅስቃሴ በማንሳት በዛሬው ጨዋታ የተሻሻለ ነገር መመልከቱን ገልጿል።
አሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረት የቡድኑን የውህደት ደረጃን በተመለከተም የሒደት ጉዳይ መሆኑን ተናግሯል።
- ማሰታውቂያ -

“ሒደት አይደለ ፤ በሒደት እስከሆነ ድረስ በሒደት የምናገኝ ይመስለኛል። ከዛ ውጪ ደግሞ በሳይኮሎጂካልም በሜዳ ላይም በልምምድ ስለምናመጣው ጊዜም ስለሚፈልግ ነው። ለፕሪሚየር ሊጉም ጥሩ ቡድን ይዘን እንቀርባለን ብዬ አስባለሁ።”
የፋሲል ከነማው ዋና አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ በበኩሉ የዚህ ወድድር ዓላማ ቡድኑ በምን ደረጃ ላይ እንዳለ ለማየት መሆኑን በማስታወስ ተጫዋቾቹ ያሉበትን ደረጃ መመልከት መቻሉም ተናግሯል።
አሰልጣኝ ዮሐንስ በጨዋታው ስለነበረው የቡድኑ እንቅስቃሴም ይህን ብሏል።
“ከዕረፍት በፊት ጥሩ ነበርን ከዕረፍት በኋላ ስህተቶች እየበዙ መጡ። አንዱ ድካም ነው ሁለተኛ አዳዲስ ልጆችም የምናይበት ስለሆነ በጣም ይጠቅመናል። ሌላው ደግሞ ሒደት ስለሆነ ቀስ እያልን እየገነባን የምንሰራው ስራ ነው።”
ከቀዳሚው የቅዱስ ጊዮርጊስ ጨዋታ ቡድኑ በዛሬው ዕለት የነበረውን የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ በማነፃፀርም አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ የተሻሻሉ ነገር እንዳሉ ገልጸዋል።
“የመጀመሪያው አጋማሽ ላይ የጨዋታ ስልታችን ጥሩ ነበረ። የምንሞክራቸው የመሀል ሜዳ ልጆች የምንሰጠውን እየሰሩ ነው። አንዳንዴ መዘናጋቶች አሉ። ያ ተሻሽሏል። ከዕረፍት በፊት ምንም አልሞከሩም አንድም ኳስ ወደ ጎላችን የሞከሩት የለም። ያ ለኛ መሻሻል ነው። ባለፈው ጨዋታ ብዙ ኳሶችን ሰጥተናል ፤ በአሁኑ ግን አልሰጠንም። የመጨረሻ አስራ አምስት እና ሀያ ደቂቃ ደግሞ መዳከም ሲመጣ ክፍተት መጣ እነኛን ሁለተኛው አጋማሽ ላይ መስራት አለብን ማለት ነው። ሁለተኛ አጋማሽ ግን በጥሩ ሁኔታ ጨርሰናል ብዬ ነው የማስበው።”
አሰልጣኝ ዮሐንስ ስለ ተከላካይ ክፍሉ በሰጠው ሀሳብም በተለይም ምኞት ደበበን በመጥቀስ በህመም ላይ መቆየቱን እና በቦታው ሌላ ሰው ስሳልነበረ ጨዋታውን እንዲጨርስ መገደዱን በመግለፅ ያ ደግሞ ዋጋ ያስከፍላል ሲሉ ተናግረዋል።
ፋሲል ከነማ በሁለቱ ጨዋታዎች ሰባት ግቦችን ያስተናገደ ሲሆን በጨዋታዎቹ የነበሩት ስህተቶች መስተካከል የሚችሉ ስለመሆናቸው ገልጸዋል።
አሰልጣኙ በቀጣይ ባሉ ክፍተቶች ላይ ተጫዋቾች እንዲመጡ ፍላጎት እንዳላቸው በመግለጽ ነገር ግን ውሳኔው የክለቡ መሆኑን እና አመራሮቹም ችግሮቹን እያዩ ስለሆነ ይቀረፋሉ ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።


