በዘጠነኛ ሳምንት የሶስተኛው ቀን ውሎ የመጀመሪያ ጨዋታ በሰበታ ከተማ እና በወልቂጤ ከተማ መካከል ተደርጎ በጳውሎስ ጌታቸው የሚመራው ወልቂጤ ከተማ 3 ለ 2 በሆነ ውጤት አሸንፏል ።
ሰበታ ከተማ በስምንተኛው ሳምንት ጨዋታ ጅማ አባጅፋር በረቱበት ጨዋታ ከነበረው ቋሚ አስራአንድ አንድ ቅያሪ ብቻ በማድረግ ሀምዛ አብዱልመንን ወደ ጨዋታው ሲያስገቡ በወልቂጤ ከተማ በኩል ደግሞ በኢትዮጵያ ቡና በተሸነፉበት ጨዋታ ከተጠቀሙት ቋሚ አሰላለፍ የስድስት ተጫዋቾች ቅያሪ ያደረጉ ሲሆን ተጫዋቾቹም ሰይድ ሀብታሙ ፤ ዮናታን ፍስሀ ፤ ዳግም ንጉሴ ፤ ሙሉጌታ ወልደጊዮርጊስ ፤ ጫላ ተሺታ እና አህመድ ሁሴን ናቸው ።

በጥሩ የሜዳ ላይ ፉክክር የተጀመረው ጨዋታ ግብ ለማስተናገድ ዘጠኝ ያህል ደቂቃዎች ነበር የቆየው ። ከሰበታ ከተማ በረጅም የተመታውን ኳስ ወጥቶ የተቆጣጠረው የወልቂጤ ከተማው ግብ ጠባቂ ሰይድ ሀብታሙ ኳሱን በረጅም በሚመታበት ጊዜ ያገኘው ሃይለሚካኤል አደፍርስ በግንባር ገጭቶ ለለአለም ብርሀኑ ለማቀበል ሲሞክር አህመድ ሁሴን ቀድሞ ኳሱን አግኝቶ በማስቆጠር ወልቂጤ ከተማን መሪ አደረገ ።

ከግቡ በኋላ ጨዋታው በአመዛኙ ሰበታ ከተማዎች ከተጋጣሚያቸው በተሻለ ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል በመድረስ ክፍተቶችን ለመፍጠር የሞከሩ ሲሆን በአንዳንድ አጋጣሚዎችም ከቆሙ ኳሶች የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ጥረቶችን ማድረግ ችለዋል ። 14ኛ ደቂቃ ላይ ከጨረቃዋ ቅርብ ርቀት ላይ የተገኘውን የቅጣት ምት ሳሙኤል ሳሊሶ መቶት የግቡ አግዳሚ መልሶበታል ። ከሁለት ደቂቃዎች በኋላም ሰበታ ከተማዎች አቻ መሆን የቻሉበትን ግብ አስቆጠሩ ።

16ኛ ደቂቃ ላይ በጥሩ ቅብብል ወደ ከቀኝ መስመር ወደ ግብ ክልል የደረሰው ኳስ በሳሙኤል ሳሊሶ አቀባይነት እና በፍፁም ገብረማርያም አስቆጣሪነት ኳሱ ከመረብ ተገናኝቷል ። ሰበታ ከተማዎች በተለይም በወልቂጤ ከተማ የግራ መስመር በኩል በተደጋጋሚ ገብተው የግብ ዕድሎችን ለማግኘት ጥረው ነበር ።
21ኛው ደቂቃ ላይ ሳሙኤል ሳሊሶ ከመሀል ክፍል የተቀበለውን ኳስ ለብቻው ከግብ ጠባቂው ጋር ተገናኝቶ በአናቱ አሳልፎ ለማስቆጠር ሲሞክር ወደ ውጪ ወቶበታል ።

በወልቂጤ ከተማ በኩል በተለይም የመሀል ክፍሉ ክፍተት በቀላሉ ከፊት መስመር ላሉ ተጫዋቾች ኳስ እንዳይደርስ አድርጓል ።
29ኛው ደቂቃ ላይ ከጌታነህ ከበደ ጥሩ ኳስ ደርሶት የነበረው አህመድ ሁሴን ኳሱን መቆጣጠር ባለመቻሉ ሊያመልጠው ችሏል ።
የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ ሁለት ያህል ደቂቃዎች ሲቀሩት አህመድ ሁሴን በሳጥን ውስጥ ሆኖ ከቀኝ መስመር የተላከለትን ኳስ ለማግኘት ሲሞክር አንተነህ ተስፋዬ በሰራበት ጥፋት ወልቂጤ ከተማዎች የፍፁም ቅጣት ምት አግኝተዋል ። የፍፁም ቅጣት ምቱንም አምበሉ ጌታነህ ከበደ 45ኛ ደቂቃ ላይ ማስቆጠር ችሏል ።

በሁለተኛው አጋማሽ በመመራት ላይ የነበሩት ሰበታ ከተማዎች በኳስ ቁጥጥሩ የተሻለ ብልጫን በመውሰድ የአጋማሹን የመጀመሪያ ደቂቃዎች አሳልፈዋል ። ነገር ግን ኳሱን መያዝ ቢችሉም የወልቂጤ ከተማን የተከላካይ መስመር አልፈው ለመግባት ተቸግረው ነበር ። ይባስ ብሎም 59ኛው ደቂቃ ላይ ሌላ ግብ አስተናገዱ ።

የመጀመሪያውን ግብ ያስቆጠረው አህመድ ሁሴን በቀኝ መስመር በኩል በወልቂጤ ከተማ ተጫዋቾች ጥሩ ቅብብል የደረሰውን ኳስ አክርሮ ወደ ግብ በመምታት ለወልቂጤ ከተማ ሶስተኛ ለራሱ ደግሞ ሁለተኛውን ግብ አስቆጠረ ።
ሰበታ ከተማዎች ቅያሪዎችንም በማድረግ የፊት መስመሩን እና የመሀል ክፍሉን በማጠናከር ግብ ለማግኘት በተደጋጋሚ ወደ ወልቂጤ ከተማ የግብ ክልል መድረስ ቢችሉም የግብ ሙከራዎችን ለማድረግ ቀደም ባሉት የጨዋታው ጊዜያቶች እንደነበረው ተቸግረው ነበር ።

69ኛ ደቂቃ ላይ በሰበታ የግራ መስመር በኩል ወደ ሳጥሰ የተላከውን ኳስ ዱሬሳ ሹቢሳ ወደ ግብ ቢሞክረውም ኢላማውን ሳይጠብቅ ወደ ውጪ ወቶበታል ። መደበኛው የጨዎጊዜ ሊጠናቀቅ 6 ያህል ደቂቃዎች ሲቀሩት በጨዋታው ጥሩ ሲንቀሳቀስ የነበረው ሳሙኤል ሳሊሶ ከርቀት የተገኘውን የቅጣት ምት አሻማው ተብሎ ሲጠበቅ አክርሮ ቀጥታ ወደ ግብ የመታውን ኳስ ሰይድ ሀብታሙ ለመቆጣጠር ባለመቻሉ ኳሱ ከመረብ ላይ አርፏል ።
ጨዋታው ከዚህ ግብ በኋላ ቀዝቀዝ ብሎ በቀሪዎቹ ደቂቃዎች ሌላ ተጨማሪ ግብ ሳያስተናግድ በወልቂጤ ከተማ አሸናፊነት ሊጠናቀቅ ችሏል ።

ውጤቱን ተከትሎም ወልቂጤ ከተማ ነጥቡን 15 በማድረስ ወደ 2ኛ ደረጃ ከፍ ሲል ሰበታ ከተማ በነበረው 7 ነጥብ የነበረበት 15ኛ ደረጃ ላይ ለመቆየት ተገዷል ።
አስተያየት ይስጡ