የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት ተደርገዋል።
በዕለቱ ቀዳሚ መርሐግብር የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን በወላይታ ድቻ 1 ለ 0 ተሸንፏል።
በጨዋታው 6ኛ ደቂቃ ላይ ፀጋዬ ብርሀኑ ያስቆጠረው ግብ ወላይታ ድቻን አሸናፊ ለማድረግ በቂ ነበር።
ፀጋዬ ብርሀኑ ግቡን ያስቆጠረው ቴዎድሮስ ታፈሰ ከማዕዘን ያሻገረውን ኳስ በግንባር በመግጨት ነው።
- ማሰታውቂያ -
ከተከታያቸው ያላቸውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሰባት የማስፋት ዕድል የነበራቸው መድኖች በቀጣዮቹ የጨዋታው ደቂቃዎች ውጤቱን ለመቀየር ያደረጉት ጥረት ውጤታማ አልሆነም።
ወላይታ ድቻ ድሉን ተከትሎ ነጥቡን 27 አድርሶ በጊዜያዊነት 7ኛ ደረጃ ላይ ለመቀመጥ ሲችል 35 ነጥቦችን የሰበሰበውን መድን ከሀድያ ሆሳዕና በአራት ነጥቦች ርቆ በመሪነቱ ቀጥሏል።
ሁለቱ ቡድኖች ከሰባት ጨዋታዎች በፊት በተመሳሳይ ስታድየም ባደረጉት ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን 2 ለ 1 አሸንፎ እንደነበር አይዘነጋም።
በ21ኛው ሳምንት መርሐግብር ኢትዮጵያ መድን ከድሬዳዋ ከተማ እንዲሁም ወላይታ ድቻ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ይጫወታሉ።
በዕለቱ ሁለተኛ መርሐግብር ከአመሻሽ 12:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ አርባምንጭ ከተማ ፋሲል ከነማን በተመሳሳይ 1 ለ 0 ረቷል።
ከቅዱስ ጊዮርጊስ በውሰት ውል አርባምንጭ ከተማን የተቀላቀለው ታምራት ኢያሱ ጨዋታው በጀመረ በ117ኛው ሰከንድ ኳስ እና መረብን አገናኝቷል።
ግቡን ሲያስቆጥር ማልያውን በማውለቁ ምክንያት የማስጠንቀቂያ የቢጫ ካርድ የተመለከተው ታምራት በ15ኛው ደቂቃ ላይ በማርቲን ኪዛ ላይ በሰራው ጥፋት በሁለተኛ የቢጫ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል።
አፄዎቹ በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ላይ በተደጋጋሚ ወደ አርባምንጭ ከተማ የግብ ክልል ለመድረስ ቢጥሩም የአርባምንጭ ከተማ የኋላ መስመር ይህን የፈቀደ አልነበረም።
በተከታታይ ሶስት ጨዋታዎች ከድል ጋር ተራርቀው የነበሩት አርባምንጭ ከተማዎች ዳግም ከድል ጋር የተገናኙበት ጨዋታም ሆኗል።
አዞዎቹ በመጀመሪያው ዙር ጨዋታም አበበ ጥላሁን በ5ኛው ደቂቃ ላይ ባስቆጠረው ብቸኛ ግብ በተመሳሳይ 1 ለ 0 ማሸነፋቸው ይታወሳል።
አዞዎቹ ማሸነፋቸውን ተከትሎም ነጥባቸውን 27 በማድረስ የ6ኛን ደረጃን በጊዜያዊነት መቆናጠጥ ችለዋል።
በቀጣይ ሳምንት መርሐግብር ፋሲል ከነማ ከባህርዳር ከተማ እንዲሁም አርባምንጭ ከተማ ከአዳማ ከተማ ይጫወታሉ።


