በሳምንቱ የመጨረሻ ቀናት የተደረጉ ጨዋታዎች አራቱም በመሸናነፍ ተጠናቀዋል።
ምድረገነት ሽረ 2-1 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
ሜዳ ላይ ከሚታዩ እንቅስቃሴዎች በስተቀር የመጀመሪያው አጋማሽ በጎል ሙከራዎች የጎመራ አልነበረም። ከዕረፍት መልስ ግን ሦስት ጎሎች የተቆጠሩበት ጨዋታ ምድረገነት ሽረዎች መሪ መሆን የቻሉት 48ኛው ደቂቃ ላይ ነበር። ንግድ ባንኮች ለማጥቃት ሳጥን ተገኝተው የተነጠቁትን ኳስ በረጅሙ ወደ ተጋጣሚ ሜዳ ተጥሎለት አጥቂው ዳንኤል ዳርጌ የግል ጥረቱን በመጠቀም ለቡድኑ ቀዳሚዋን ግብ መረቡ ላይ አዋህዷል።
ጨዋታው በእንቅስቃሴዎች እየታጀበ ጭማሪው ደቂቃ ላይ እንደደረሰ ንግድ ባንኮች ወደ ጨዋታ የመለሳቸውን ጎል አግኝተዋል። በጥሩ የእግር ስራ 90+3 ደቂቃ ላይ አዲሱ መገርሳ ከቀኝ የሳጥኑ ክፍል የሰጠውን ናትናኤል ዳንኤል የአቻነት ግብ ማድረግ ችሏል። ጨዋታው በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ ሲባል ሽረን ያስፈነጠዘ አጋጣሚ ተፈጥሯል። 90+5 ደቂቃ ላይ ሽመክት ጉግሳ ከማዕዘን ሲያሻማ በበሀይሉ ግርማ እና በሌሎች ተጫዋቾች ተገጫጭታ የደረሰችውን ከመቻል ሽረ በአጋማሹ ዝውውር የደረሰው ደሳለኝ ከተማው በግንባር በመግጨት ግብ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ፋሲል ከነማ 1-2 ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርስቲ
የመጨረሻ ደቂቃ ጎል ወልዋሎን አሸናፊ ማድረግ የቻለው የአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ስታዲየም የምሽቱ መርሀግብር ፋሲሎችን በመጀመሪያው አጋማሽ 40ኛው ደቂቃ ላይ ቀዳማ ያደረገ ነበር። ከእጅ ውርወራ የተነሳችውን ኳስ የወልዋሎ ተከላካይ ኪሩቤል ወንድሙ በግንባር ገጭቶ ጃቢር ሙሉ ያገኛትን ኳስ በአስደናቂ ቮሊ መረቡ ላይ አሳርፏታል።
ከዕረፍት መልስ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ብርቱ ጥረት ያደረጉት ወልዋሎዎች ወደ ጨዋታው ተመልሰዋል። በጥሩ ቅብብል 60ኛው ደቂቃ ሳጥን ውስጥ ዳዊት ገብሩ ወደ ውስጥ የሰጠውን ኳስ ኤፍሬም ሀይለማርያም ሳይቸገር አቻ ያደረገች ጎል አድርጓታል። ጨዋታው ቀጥሎ በተሰጠው ጭማሪ ደቂቃ ላይ በረጅሙ ከተከላካይ ጀርባ የተጣለን ኳስ የምኞት ደበበ ስህተት ታክሎ ጋናዊው አጥቂ ኮንኮኒ ሀፊዝ ለወልዋሎ ውድ ሦስት ነጥብ ያስገኝ ጎልን አክሎ ጨዋታው 2ለ1 በሆነ ውጤት ተቋጭቷል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ 0-1 ሀድያ ሆሳዕና
በብዙ ረገድ በሙከራዎች ያልደመቀ ቆይታ የነበረው በፀሀያማ አየር የተደረገው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በሀድያ ሆሳዕና አሸናፊነት ተቋጭቷል። ተመጣጣኝ በሚመስል እንቅስቃሴ እና ሙከራዎች የተደረጉበት ጨዋታ በሁለተኛው አጋማሽ መጠነኛ መሻሻልን ያሳዩት ሀድያ ሆሳዕናዎች ድል አድርገዋል። በጥሩ ሽግግር 79ኛው ደቂቃ ላይ ጫላ ተሺታ ከቀኝ ወደ ውስጥ የሰጠውን ኳስ ደስታ ዋሚሾ ከመረብ አዋህዶ ጨዋታው 1ለ0 በነብሮቹ የበላይነት ተጠናቋል።
ባህርዳር ከተማ 0-2 አርባምንጭ ከተማ
የባህርዳር ከተማ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ የታየበት እና የአርባምንጭ ከተማ ከፍ ያለ ተነሳሽነት እና የመልሶ ማጥቃቶች የታጀበው ጨዋታ አዞዎቹን አሸናፊ ያደረጉ ጎሎች የተገኙት በመጀመሪያው አጋማሽ ላይ ነበር። 19ኛው ደቂቃ ላይ ኤፍሬም ታምራት ከግራ የላካትን ኳስ ቡጣቃ ሸመና ጎል በማድረግ አዞዎቹን መሪ አድርጓል። 31ኛው ደቂቃ ላይ ጄሮም ፒሊፕ ያቀበለውን ኳስ ወጣቱ ይድነቃቸው ያሲን በድንቅ አጨራረስ ሌላ ጎል በማስቆጠር ከደረጃ ግርጌው ለመውጣት ለሚጣጣረው ክለብ ተጨማሪ ጎል በማድረግ ጨዋታው ተቋጭቷል።


