በሳምንቱ የሁለተኛ ቀን ጨዋታ በጎል የጎመራው የሸገር እና አዳማ ጨዋታ 3ለ3 በሆነ የአቻ ውጤት ሲቋጭ መቻል ከ መቐለ ያለ ጎል ድቻ እና ቡናማዎቹ በድል ቋጭተዋል።
ሸገር ከተማ 3-3 አዳማ ከተማ
ሀዋሳ ላይ ሁለቱን የኦሮሚያ ክለቦች ያገናኘው ጨዋታ በሚገርም የሜዳ ላይ ፉክክር ታጅቦ በመጨረሻም በአቻ ውጤት መጠናቀቅ ችሏል። በመጀመሪያዎቹ አስር ደቂቃዎች ጥሩ ለመንቀሳቀስ የቻሉት አዳማዎች 10ኛው ደቂቃ በጥሩ ቅብብል ከቀኝ አቡበከር ሳኒ የሰጠውን ኳስ ተጠቅሞ አህመድ ሁሴን ከመረብ በማሳረፍ አዳማን መሪ ማድረግ ችሏል። ከዕረፍት መልስ በይበልጥ ተሻሽለው የቀረቡት ሸገሮች 60ኛው ደቂቃ ናትናኤል ዘለቀ ከብዙአየው ሰይፈ የነጠቀውን ኳስ ከፍ አድርጎ የሰጠውን ኳስ ቢኒያም ፍቅሬ በጥሩ አጨራረስ ከመረብ በማሳረፍ ቡድኑን አቻ ማድረግ ችሏል።
በቀጣዮቹም ደቂቃዎች በርካታ የግብ ዕድሎችን በመፍጠሩ የተዋጣላቸው ሸገሮች እጅግ የሚያስቆጩ ዕድሎችን ቢያገኙም በቀላሉ ሲያመክኑ ተስተውሏል። 87ኛው ደቂቃ ጀቤሳ ሜኤሳ ከተከላካይ ጀርባ የተጣለለትን ኳስ በድንቅ አጨራረስ ከተመሪነት ወደ መሪነት ክለቡን ማሸጋገር ችሏል። አዳማ ከተማዎች መንቃቅን በጀመሩበት የመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች 90+1 ላይ ከጉዳት የተመለሰው አላዛር ሽመልስ ከሳሙኤል ዮሐንስ የተሻገረውን ኳስ በግንባር ገጭቶ አዳማን ወደ ጨዋታ የመለሰ ሲሆን አሁንም አላዛር እጅግ አስደናቂ ሌላ ጎል በማከል አዳማን ወደ መሪነት ማሸጋገር ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ጨዋታው ሊጠናቀቅ በቀሩት ሽርፍራፊ ሰከንዶች ውስጥ ለአዳማ ሁለት ጎል ያስቆጠረው አላዛር ሽመልስ በራሱ የጎል ክልል ኳስን በእጅ በመንካቱ የተሰጠውን የፍፁም ቅጣት ምት ሔኖክ አዱኛ ከመረብ አሳርፎት በመጨረሻም ጨዋታው 3ለ3 ሊጠናቀቅ ግድ ብሏል።
ነገሌ አርሲ 0-1 ኢትዮጵያ ቡና
እጅግ ጠንካራ ፉክክርን ያስተዋልንበት የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ የምሽቱ መርሀግብር በበርካታ ደጋፊዎች የታጀበ ነበር። ነገሌዎች በተሻለ መንቀሳቀስ የቻሉበት የመጀመሪያው አጋማሽ በመከራ ረገድ ግን ቡናማዎቹ ሻል ያሉበት እንደነበር ተስተውሏል። ከዕረፍት መልስ ነገሌዎች ጥሩ አጀማመር ለማድረግ ጥረቶች ያልተለያቸው ቢሆንም የኋላ ኋላ ግን ኢትዮጵያ ቡናዎች በሽግግር የዋዛ አልነበሩም።
በዚህም የተነሳ 87ኛው ደቂቃ ተቀይሮ የገባው ኤርሚያስ ሹምበዛ ወደ ሳጥን ከግራ ሲያሻማ ቦና ቦካ በእጅ ኳስን በመንካቱ የተሰጠውን የፍፁም ቅጣት ምት የቡናማዎቹ አምበል ራምኬል ጀምስ ከመረብ አዋህዶ ቡድኑን አሸናፊ አድርጓል።
ድሬዳዋ ከተማ 0-2 ወላይታ ድቻ
ወላይታ ድቻ ተከታታይ ሁለተኛ ድሉን አሳክቷል። ተመጣጣኝ የሚመስል መልክ ከነበረው የመጀመሪያው አጋማሽ በሁለተኛው በአንፃራዊነት ድቻዎች የተሻሉ ነበሩ ለዚህም መነሻው 49ኛው ደቂቃ ላይ የድሬዳዋው ድልአዲስ ገብሬ መሳይ ኒኮል ላይ በሰራው አደገኛ ጥፋት በቀይ ካርድ መውጣቱ ቡድኑ የጎዳው መስሏል።
65ኛው ደቂቃ የቁጥር ብልጫን የያዙት የጦና ንቦቹ ካርሎስ ዳምጠው ከሳጥን ውጪ አስደናቂ ጎል በማስቆጠር ቡድኑ መሪ አድርጓል። 83ኛው ደቂቃ ያሬድ ዳርዛ ከግራ ወደ ውስጥ አሻምቶ ዮናታን ኤልያስ የተከላካዮች ስህተት ታክሎ ካርሎስ ዳምጠው ጋር የደረሰችውን ኳስ ለራሱም ለቡድኑም ሁለተኛ ጎል በማድረግ ጨዋታው 2ለ0 መጠናቀቅ ችሏል።
መቻል 0-0 መቐለ 70 እንደርታ
በመጀመሪያው አጋማሽ ተመጣጣኝ በሁለተኛው አጋማሽ ደግሞ መቻሎች የተሻለውን ቆይታ ያሳዩበት የአዳማው የምሽት ጨዋታ ያለ ጎል ተቋጭቷል።


