ፋሲል የመጀመሪያ ሽንፈቱን በኢትዮጵያ ቡና ሲያስተናግድ የጣና ሞገዶቹ እና መድን ድል አድርገዋል።
መቻል 1-2 ባህርዳር ከተማ
የጣናውን ሞገድ ከ ጦሩ ያገናኘው የሳምንቱ የሁለተኛ ቀን የአዲስ አበባ ስታዲየም የዕለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ማኑሄ ወልደፃዲቅ የተመራ ነበር። ባህርዳር ከተማዎች በብዙ ረገድ ብልጫውን በወሰዱበት የመጀመሪያው አጋማሽ ገና 6ኛው ደቂቃ ላይ ያለቀለት አጋጣሚን መፍጠር ችለዋል። ኩዋቤና ቦአቲንግ ከቀኝ ወደ ውስጥ ያሻገራትን ኳስ ወንድወሰን በለጠ ከግብ ጠባቂው ምንታምር መለሠ ጋር ተገናኝቶ ሳይጠበቅ ያባከነበት እና ወንድወሰን በለጠ በድግግሞሽ ያመከናቸው ሌሎች የግብ ዕድሎች የሚያስቆጩ ነበሩ።
መከላከል ላይ በአመዛኙ ለማሳለፍ የተገደዱት እና በይበልጥ በፈጣን ቅብብል ከራሳቸው ሜዳ ለመውጣት ውስንነት ይታይባቸው የነበሩት መቻሎች 37ኛው ደቂቃ ላይ በተጋጣሚያቸው ሌላ አደገኛ ሙከራን አስተናግደዋል። ወንድወሰን በለጠ የግል ጥረቱን ተጠቅሞ ከግራ የሳጥኑ ክፍል ወደ ቀኝ የላከለትን ኳስ ኩዋቤና ቦአቲንግ የማስቆጠር ነፃ አጋጣሚን አግኝቶ በቀላሉ አምክኗታል።
- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ ከቆሙበት የቀጠሉት ባህርዳሮች ከቆሙበት ቀጥለው ኩዋቤና ቦአቲንግ ካመከናት አጋጣሚ በኋላ ደቂቃው 57ኛው ላይ ሲደርስ ጎልን ወደ ቋታቸው ከተዋል። ግሩም ሀጎስ ቦአቴንግ ላይ የሰራውን ጥፋት ተከትሎ የተገኘን ቅጣት ምት ፍፁም ፍትህአለሙ ሲያሻማ ከወንድወሰን ሙከራ መልስ ኳሷን ያገኘው ፍቅረሚካኤል አለሙ ጎል በማድረግ ቡድኑን መሪ አድርጓል።
ተጨማሪ ጎልን ለማግኘት ብርቱ ጥረት ማድረግን የቀጠሉት የጣና ሞገዶቹ 68ኛው ደቂቃ ላይ በጥሩ አንድ ሁለት ሔኖክ ይበልጣል የሰጠውን ኳስ ከሳጥኑ ጠርዝ ግርማ ዲሳሳ የቀድሞው ክለቡ ላይ አስገራሚ ሁለተኛ ጎል አስገኝቷል። ሁለት ጎሎችን ካስተናገዱ በኋላ ዘግይተው ወደ ጨዋታ የመጡት መቻሎች በጭማሪው 90+4 ደቂቃ ላይ ቻላቸው መንበሩ ከቀኝ የላከለትን ኳስ መሐመድ አበራ በግንባር አስቆጥሮ ከማስተዛዘኛ ውጪ መሆን ያልቻለች ጎል ሆና ጨዋታው ተፈፅሟል።
ፋሲል ከነማ 0-2 ኢትዮጵያ ቡና
አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሳልፎ በመስጠቱ በረዳት አሰልጣኙ አምሳሉ እሰመለአለም እየተመራ የገባው ፋሲል ከነማ እና በአዲሱ አሰልጣኝ ሳምሶን አየለ በተቃራኒው ለመጀመሪያ ጊዜ የተመራው ኢትዮጵያ ቡና በመጀመሪያው የጨዋታ አጋማሽ ቡናማዎቹ በብዙ ረገድ የተሻሉ ቢመስልም በፈጣን ሽግግር ለመጫወት ጥረት ሲያደርጉ ያስተዋልናቸው ፋሲል ከነማዎች ገና በ5ኛው ደቂቃ ላይ ከግራ ቃልኪዳን ዘላለም በአንድ ለአንድ ግንኙነት በግብ ዘቡ እንዳሻው እሸቴ የተመለሰችበት አጋጣሚ በጥራት የተሞላችዋ የቀዳሚው አጋማሽ ሙከራ ነበረች።
በሁለተኛው አጋማሽ ከወገብ በላይ ጠጣር ሆነው የቀረቡት ኢትዮጵያ ቡናዎች 62ኛው ደቂቃ ላይ ጎል አግኝዋል። ዲቫይን ዋቹኩዋ በረጅሙ ከግራው የሜዳ ክፍል ያሻገራትን የቅጣት ምት ራምኬል ጀምስ ወደ ጎል ገጭቶ ዋሳዋ ለማውጣት ጥረት ያደረጋትን ኳስ ዘላለም አባተ አየር ላይ አግኝቷት በድንቅ የመቀስ ምት መረቡ ላይ አሳርፎ የባለፈው አመት ጎል አስታውሷል።
ከወትሮ እንቅስቃሴያቸው መጠነኛ መቀዛቀዝ የታየባቸው ፋሲሎች 74ኛው ደቂቃ ተጨማሪ ጎል አስቆጥረዋል። ዘላለም አባተ አሾልኮ የሰጠውን ኳስ ሳጥን ውስጥ በእጅ ቢነካም የዕለቱ ረዳት ዳኛ ሙሉነህ በዳዳ ደካማ የቦታ አጠባበቅ ታክሎበት አቡበከር አዳሙ መረብ ላይ አሳርፎ ጨዋታው ኢትዮጵያ ቡናን ወደ ድል ሲመልስ አፄዎቹን የአመቱ የመጀመሪያ ሽንፈት እንዲያስተናግዱ ሆኗል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 0-0 ሀድያ ሆሳዕና
ጎል ሳይቆጠርበት ለመጠናቀቅ የተገደደው እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በንፅፅር አማካይ ክፍሉ ላይ በወሰዱት የእንቅስቃሴ ብልጫ ከቅጣት ምት በአዲስ ግደይ አማካኝነት የሚያስቆጩ የቅጣት ምት አጋጣሚዎች የፈጠሩበት በአንፃሩ ሀድያ ሆሳዕና ሔኖክ አርፊጮ ከቅጣት ምት እና ብሩክ በየነ ግልፅ ዕድል ማብከን የቻሉበት ከዕረፍት መልስ 73ኛው ደቂቃ የሀድያ ሆሳዕናው አምበል ሔኖክ አርፊጮ በቀይ በሁለት ቢጫ የወጣበት ነበር።
ወላይታ ድቻ 1-2 ኢትዮጵያ መድን
አመሻሹን አዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ ሜዳ ላይ ወላይታ ድቻን ከ ወቅቱ ሻምፒዮን ኢትዮጵያ መድን ጋር ያገናኘው ጨዋታ ወላይታ ድቻዎች ከጨዋታው አንዳች ነገርን የፈለጉ በሚመስል እንቅስቃሴ ያደረጉት ጥረት 17ኛው ደቂቃ ላይ ፍሬ አፍርቶላቸዋል። አማካዩ ቴዎድሮስ ታፈሠ በጥሩ ዕይታ አሾልኮ የሰጠውን ኳስ ወጣቱ ቴዎድሮስ ታፈሠ ንጋቱ ገብረስላሴ አምልጦ በድንቅ አጨራረስ ፋሲል ገብረሚካኤል መረብ ላይ በማስቆጠር በተከታታይ ተሰላፊነት ጎልን ለክለቡ አስቆጥሯል።
ከሰላሳ ደቂቃዎች በኋላ ዘግየት ብለው ወደ ጨዋታ ቅኝት እየገቡ የመጡት መድኖች ወደ መልበሻ ክፍል ጨዋታው ሊያመራ ሦስት ያህል ደቂቃዎች ብቻ እንደቀሩ 42ኛው ደቂቃ ላይ ያሬድ ካሳዬ ከቀኝ የሜዳ ክፍል ወደ መስመር ከተጠጋ ቦታ የተገኘን የቅጣት ምት ወደ ጎን ለዳዊት አውላቸው አቀብሎት ወደ ጎን አማካዩ ሞክሮ ግብ ጠባቂው ቢኒያም ገነቱ የተፋውን ኳስ በረከት ካሌብ በግንባር ገጭቶ መረቡ ላይ አስቀምጦ ጨዋታው 1ለ1 አድርጓል።
በሁለተኛው አጋማሽ የቀጠለው የቡድኖቹ ጨዋታ ረጃጅም ኳሶችን ከጅምሩ ማየት የቻልንበት ሲሆን መድኖች በበኩላቸው ፈጣን አጀማመር ያደረጉት ነበር። 48ኛው ደቂቃ ላይ የጦና ንቦቹ ተከላካይ መልካሙ ቦጋለ በሳጥን ውስጥ ረመዳን የሱፍ ላይ የሰራውን ጥፋት ተከትሎ የተሰጠውን የፍፁም ቅጣት ምት ዩጋንዳዊው አጥቂ አለን ካይዋ ቢመታውም የግቡን አግዳሚ ኳሷ ለትማ ወጥታለች።
ተመሳሳይ የረጃጅም ኳስ አጠቃቀምን እያስተዋልን በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ያስተዋልነበት ጨዋታ 65ኛው ደቂቃ ጎል አስመልክቶናል ከጥሩ የእግር ስራ በኋላ ወደ ግራ ሳጥኑ ብሩክ በላቸው የሰጠውን ኳስ ብሩክ ሙሉጌታ በጥሩ አጨራረስ ቡድኑን ወደ 2ለ1 ያሸጋገረች ጎልን አስቆጥሮ ጨዋታው በመጨረሻም ተጠናቋል።


