አራት ጎሎች የተመዘገቡበት ሁለት ጨዋታዎች በተመሳሳይ የ1ለ1 ውጤት ተጠናቀዋል።
ወላይታ ድቻ 1-1 ምድረገነት ሽረ
ከሙከራዎች በፀዳ መልኩ ጥንቃቄ ላይ ትኩረት ባደረገ እንቅስቃሴ ብቻ የተደረገው የሁለቱ ቡድኖች ቀዳሚው አጋማሽ የመጨረሻው ሜዳ ላይ ልዩነት ሊፈጥሩ የሚችሉ ክስተቶችን ሳናስተውል ወደ መልበሻ ክፍል አምርቷል።
ከዕረፍት መልስ በእጅጉ ተሻሽሎ በተመለሰው እንዲሁም ምድረገነት ሽረዎች በሚታወቁበት የመስመር ማጥቃት ጫና መፍጠርን ቀጥለው 54ኛው ደቂቃ ላይ ከራሳቸው የግብ ክልል በረጅሙ የተላከን ኳስ ከአጥቂው ዳንኤል ዳርጌ ጋር ታግሎ ለማሸነፍ ጥረት ሲያደርግ የነበረው ናትናኤል ናሲሩ ኳስን ሳጥን ውስጥ በእጅ መነካቱን ተከትሎ የዕለቱ ዳኛ ሚካኤል ጣዕመ የሰጡትን የፍፁም ቅጣት ምት ሽመክት ጉግሳ ሲመታው ግብ ጠባቂው ቢኒያም ገነቱ እና የግቡ ቋሚ ብረትን ገጭታ ስትመለስ ሽመክት ዳግም አግኝቷት መረቡ ላይ አሳርፏታል። አሰልጣኝ መሳይ ተፈሪ ከሹመታቸው በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ወላይታ ድቻን በመሩበት ጨዋታ 88ኛው ደቂቃ ላይ ከማዕዘን ምት ቴዎድሮስ ታፈሠ ሲያሻማ ተቀይሮ የገባው ተከላካዩ አዛሪያስ አቤል በግንባር ገጭቶ በማስቆጠር ቡድኑ አንድ ነጥብን ይዞ እንዲወጣ አስችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ኢትዮጵያ መድን 1-1 ኢትዮ ኤሌክትሪክ
ሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ስታዲየም ላይ የአምናውን ሻምፒዮን ኢትዮጵያ መድን እና ኢትዮ ኤሌክትሪክን ያገናኘው ጨዋታ በመጀመሪያው አስራ አምስት ደቂቃዎች ውስጥ በተሻለ ብልጫውን ወስደው መንቀሳቀስ መርጠው የታዩት መድኖች መሪ የሆኑበት ነበር። 12ኛው ደቂቃ ላይ ከቀኝ መስመር አቅጣጫ ወጣቱ ዳዊት አውላቸው የላካትን ኳስ ሳጥኑ ጠርዝ ላይ የነበረው ተከላካዩ ያሬድ የማነ በእጅ በመንካቱ በዕለቱ ዳኛ ሙሉቀን ያረጋል የተሰጠውን የፍፁም ቅጣት ምት ረመዳን የሱፍ በቀላሉ መረብ ላይ በማሳረፍ ቡድኑን መሪ ማድረግ ችሏል። በቀጣዮቹ የጨዋታ ደቂቃዎች ተመጣጣኝ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴዎችን በሁለቱም ቡድኖች በኩል ቢስተዋልም ጥራት ያላቸው የጎል ዕድሎች ግን በይበልጥ አላስተዋልንበትም።
ከዕረፍት ጨዋታው ተመልሶ ሲቀጥል የተጫዋች ለውጥን በማድረግ ለሳጥኑ የተጠጋውን እንቅስቃሴ ማዘውተር የጀመሩት ኤሌክትሪኮች እንደነበራቸው መሻሻል ጎልን ያስቆጠሩት መደበኛው የጨዋታ ደቂቃ ሊጠናቀቅ አስር ደቂቃዎች ሲቀሩት ነበር። 81ኛው ደቂቃ ከቀኝ ወደ ውስጥ አሸናፊ ጥሩነህ ያቀበለውን የመድን ተከላካዮች መዘናጋት ታክሎበት ብቻውን ኳሷን ያገኘው ወጣቱ አብነት ተስፋዬ ወደ ግብነት ቀይሮ ጨዋታው በሁለት አጋማሾች በተቆጠሩ ጎሎች 1ለ1 በሆነ የአቻ ውጤት ተጠናቋል።


