በሳምንቱ የማሳረጊያ ቀን በተደረጉ ጨዋታዎች ምድረገነት ሽረ በድል ሲያሸበርቅ ሁለት ቀሪ ጨዋታዎች በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል።
ድሬዳዋ ከተማ 0-2 ምድረገነት ሽረ
ሳምንቱን በሚያሳርገው የዕለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ በአዲስ አበባ ስታዲየም ላይ ሲደረግ ድሬዳዋ ከተማን ከምድረ ገነት ሽረ በማገናኘት ጅምሩን አድርጓል። የሽረዎች የበላይነት በይበልጥ በተንፀባረቀበት እና በሽግግር ከመስመር በመነሳት ጥቃትን ለመሰንዘር ከተጋጣሚያቸው በተሻሉበት የመጀመሪያው አጋማሽ በተለይ ሽመክት ጉግሳ ከሁለቱ አጥቂዎች ዳንኤል ዳርጌ እና አቤል ማሙሽ ጋር ልዩ በሆነ አቀራረብ ደጋግመው ወደ ጎል መድረስ የቻሉበት ነበር። 41ኛው ደቂቃ ከሽመክት ጉግሳ ያገኘውን ኳስ ዳንኤል ዳርጌ ከመረብ ቢያሳርፍም የዕለቱ አንደኛ ዳኛ ከጨዋታ ውጪ በሚል ከሻሯት ከአንድ ደቂቃ መልስ የጨዋታው ልዩነት ፈጣሪ ሽመክት የላከለትን ኳስ ከባህርዳር ቡድኑን የተቀላቀለው አቤል ማሙሽ የቡድኑ መሪነት ያረጋገጠች ጎል አክሏል።
በመጀመሪያው አጋማሽ ደጋግመው ጫናን ከሙከራዎች ጋር ሲሰነዝሩ የነበሩት ሽረዎች ከቆሙበት መቀጠል ሲችሉ የአሰልጣኝ ይታገሱ እንዳለው ድሬዳዋ የተጫዋቾችን ለውጥ ጭምር በማድረግ ወደ ጨዋታ ለመመለስ ጥረት ቢያደርጉም በመከላከሉ ይሰሯቸው በነበሩ ስህተቶች ጎልን አስተናግደዋል። 65ኛው ደቂቃ ላይ የሽመክት ጉግሳ ድንቅ የማቀበል ጥረት ታክሎበት ዳንኤል ዳርጌ ከመረብ አዋህዶ ጨዋታው በምድረ ገነት ሽረ 2ለ0 አሸናፊነት ተቋጭቷል።
- ማሰታውቂያ -
መቐለ 70 እንደርታ 2-2 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
መቐለን 70 እንደርታን ከ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አገናኝቶ የነበረው ቀጣዩ መርሀግብር በአቻ ውጤት ተቋጭቷል። ኪቲካ ጀማ ከወጣቱ አማካይ በዛብህ ካቲሶ ያገኘውን ኳስ መረብ ላይ አስቀምጦ ቡድኑን መሪ ቢያደርግም ለዕረፍት ጨዋታው ለመውጣት ሲቃረብ ዩጋንዳዊው አጥቂ ሳይመን ወደ ግብ መቶ በሶፎኒያስ ሰይፈ የተመለሰች ኳስን የቀድሞው የንብ አጥቂ ኤፍሬም ሌጋሞ የአቻነት ግብ አድርጓታል።
ከዕረፍት መልስ ንግድ ባንኮች በፈጣን እንቅስቃሴ ወደ ሜዳ መመለስ በቻሉበት ቅፅበት አዲስ ግደይ ከሳይመን ፒተር የተላከለትን ኳስ ወደ ጎልነት ቀይሮ ቡድኑን ወደ 2ለ1 ማሸጋገር ቢችልም 80ኛው ደቂቃ ላይ አሰጋኸኝ ጴጥሮስን በቀይ ካርድ ያጡት መቐለዎች ተጨማሪ ጎልን የሚያስተናግዱ ቢመስሉም በጭማሪው 90+5 ደቂቃ ላይ ሱለይማን ሀሚድ ከቅጣት አሻምቶ በናትናኤል ዳንኤል ተጨርፋ ወደ ጎልነት ተለውጣ በመጨረሻም ጨዋታው 2ለ2 በሆነ ውጤት ተጠናቋል።
ሀድያ ሆሳዕና 1-1 አርባምንጭ ከተማ
የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ እንዲሁም የሳምንቱ የማሳረጊያ ጨዋታ በመጨረሻ ደቂቃ ጎል 1ለ1 መጠናቀቅ ችሏል። የመጀመሪያዎቹ የጨዋታ ደቂቃዎች በተሻለ የማጥቃት ደመ ነብስ ልዩነት ለመፍጠር ጥረት ሲያደርጉ የነበሩት አርባምንጭ ከተማዎች 11ኛው ደቂቃ ከማዕዘን ምት ኤፍሬም ታምራት ያሻረውን ኳስ ታምራት እያሱ በግንባር በመግጨት ያስቆጠራት ጎል አዞዎቹን መሪ መሆን እንዲችሉ አድርጋለች።
ከዕረፍት መልስ የተጫዋች ለውጥን ጭምር በማድረግ ከተመለሱ በኋላ የአርባምንጭ የመጨረሻው ሜዳ ላይ መዋል የቻሉት ሀድያ ሆሳዕናዎች 84ኛው ደቂቃ ከመስመር የተሻማን ኳስ እዮብ አለማየሁ በግንባር በመግጨት አስቆጥሮ ሀድያ ሆሳዕና 1ለ1 ሆኖ እንዲጨርስ አድርጓል።


