የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም የዛሬ ጨዋታዎች ሀዋሳ ከተማን ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 1ለ1 መቻልን ደግሞ ከፋሲል ከነማ ያለ ጎል ለያይቷል።
ሀዋሳ ከተማን ከ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያገናኘው ጨዋታው በመጀመሪያዎቹ ሰላሳ ደቂቃዎች ወደ መስመሮች በኩል አጋድለው መጫወትን መርጠው የታዩት ሐይቆቹ 24ኛው ደቂቃ ላይ በተጋጣሚያቸው የቅብብል ስህተት ጎል አስቆጥረዋል። ተባረክ ሄፋሞ ከብሩኩ ብፁአምላክ እግር ላይ የነጠቀውን ኳስ ለወጣቱ ያሬድ ብሩክ ሰጥቶት አማካዩ ከሳጥን ውጪ አክርሮ በመምታት የግብ ዘቡ ፓላክ ቾል የአያያዝ ስህተት ታክሎበት ኳሷ መረብ ላይ አርፋለች።

ጎል ካስቆጠሩ በኋላም ለተጨማሪ ጎል በጌታነህ ከበደ እና ያሬድ ብሩክ ጥቃት የሰነዘሩት ሀዋሳዎች በተለይ ያሬድ ብረት የመለሰበት አጋጣሚ ተጠቃሿ ሙከራቸውም ነበረች። በቀጣዮቹ ደቂቃ ንግድ ባንኮች ወደ ጨዋታ ቅኝት ለመመለስ ባደረጉት ጥረት የመቻል ሳጥን ጠርዝ ወንድማገኝ ማዕረግ ጥፋት በመስራቱ የተገኘውን የቅጣት ምት አዲስ ግደይ በድንቅ ብቃት በማስቆጠር ወደ አቻነት አሸጋግሯል።
- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ በንፅፅር በእንቅስቃሴ ብልጫን ለመውሰድ ቡድኖቹ ከሚያደርጉት ጥረት በስተቀር ብዙም የተሳኩ የማጥቃት ደመ ነብስን መመልከት አልቻልንም።

ሊጉ የከተማ ለውጥን እስኪያደርግ ወደ ዕረፍት ከማምራቱ በፊት የመጨረሻ በሆነው የሳምንቱ የማሳረጊያ ጨዋታ ከጅምሩ እስከ ፍፃሜው በፉክክሮች የተሞላ ቢሆንም ጥራት ያላቸውን ዕድሎችን ግን ያላስዋልንበት ነበር። በመጀመሪያው አጋማሽ በመቻል በኩል የቸርነት ጉግሳን አደገኛ ኳስ የግብ ዘቡ ሞይስ ፓዎቴ ያወጣበት እና በፋሲሎች በኩል ደግሞ ከማዕዘን ተሻምቶ ያሬድ ብርሀኑ በግንባር ገጭቶ ያደረጋት ሙከራ ከዕረፍት መልስ የመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ፋሲሎች በበረከት ግዛው ተደጋጋሚ ጥቃትን መቻሎች በበረከት ደስታ ያለቀለት ሙከራን ሰንዝረው የግብ ዘቡ ሞይስ ያመከናቸው ጥቂት አጋጣሚዎችን በጨዋታው ማስተዋል ቢቻልም ጎል ሳይቆጠርበት በመጨረሻም ፍፃሜን አግኝቷል።


