በሀዋሳ ዩኒቨርሰቲ ስታዲየም በተደረጉ የሳምንቱ መባቻ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና መቻል በድል አጠናቀውበታል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 2-0 ድሬዳዋ ከተማ
ተመጣጣኝ አጀማመር በነበረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ፈጣን አጀማመርን ያደረጉት ንግድ ባንኮች በመጀመሪያው አጋማሽ አዲስ ግደይ በጥሩ ዕይታ ሰጥቶት ብሩክ ብፁአምላክ ቋሚ ብረቱ በመለሰበት አጋጣሚ አስደንጋጭ ሙከራን በማድረጉ ቀዳሚ ነበሩ።። በእንቅስቃሴ በተወሰነ ረገድ ይበለጡ እንጂ በጥልቅ አጨዋወት ሙከራን ከማድረግ ያልቦዘኑት ድሬዎች መስዑድ ከቅጣት አሻምቶ ተጨራርፋ የግብ ዘቡ ፓላክ ቾል ያወጣት እና አብዱሰላም የሱፍ ነፃ አጋጣሚን አግኝቶ ሳይጠቀም የቀረበት ተጠቃሾቹ ሙከራዎች ሆነዋል።
ተጋጣሚያቸው ሲያጠቃ መከላከሉን በአግባቡ መቆጣጠር ላይ ውስንነቶች የነበሩባቸው ድሬዎች 42ኛው ደቂቃ በፈጣን መልሶ ማጥቃት ሳይመን ፒተር ጎል አስቆጥሮ ሀምራዊ ለባሾቹን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል። ጎልን ካስቆጠሩ በኋላ ይበልጥ መነቃቃት የቻሉት ንግድ ባንኮች ተጨማሪ የግብ ዕድልን ቢያገኙም ወደ ጎልነት መለወጥ ሳይችሉ አጋማሹ ተገባዷል።
- ማሰታውቂያ -

ከዕረፍት መልስ ጨዋታው ሲመለስ ይበልጥ የድሬዳዋ ከተማ ሦስተኛው የሜዳ ክፍል ላይ ደጋግመው የሚገኙት ንግድ ባንኮች በርካታ የጎል ዕድሎችን አግኝቶ የተከላካዩ አህመድ ረሺድ አስደናቂ አቋም ታክሎበት ድሬዳዋ በርካታ ጎሎችን ከማስተናገድ የተረፈበትን ሂደት አስተውለናል። አዲስ ግደይ በሰጠው እና ሳይመን ፒተር ባመከናት ሙከራ ማጥቃታቸው የጀመሩት ንግድ ባንኮች ከቀኝ መስመር አቅጣጫ ወደ ውስጥ 77ኛው ደቂቃ ላይ የተሻማን ኳስ አስቻለው ታመነን ተክቶ ወደ ሜዳ የገባው ድልአዲስ ገብሬ ራሱ ላይ አስቆጥሮ አዲስ ግደይ ደግሞ ብረት ከመለሰበት ዕድል በኋላ በመጨረሻም ጨዋታው በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 2ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።
ወልዋሎ ዓ/ዩኒቨርስቲ 0-2 መቻል
በአሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረት የሚመራው መቻል በመጀመሪያው አጋማሽ ጨዋታው ሙሉ በሙሉ መቆጣጠር የቻለ ሲሆን ከአማካይ ክፍሉ ስርጭት ወደ መስመር አጋድሎ በሚደረግ እንቅስቃሴ ጎልን ያስቆጠሩት ገና አስረኛው ደቂቃ ላይ ነበር። ከአብዱልከሪም ያገኘውን ግሩም ሐጎስ ወደ ጎል ኳሷን ሲመታ መሐመድ አበራ አግኝቶ በቄንጠኛ አጨራረስ መረቡ ላይ አሳርፎ መቻል መሪ መሆን ችሏል። በእንቅስቃሴ ብልጫውን እየወሰዱ መጓዙን መርጠው የታዩት መቻሎች 36ኛው ደቂቃ በረከት ደስታ ቀኝ ሳጥን ቦታ ወደ ውስጥ ያሻማውን ኳስ ብሩክ ማርቆስ በግንባር ገጭቶ ሁለተኛ ጎል አድርጎታል።
በሁለተኛው አጋማሽ እጅግ ተሻሽለው ወደ ጨዋታ ለመመለስ በእጅጉ ጥረት ሲያደርጉ የታዩት ወልዋሎች ጥቂት የማይባል ዕድልን ማግኘት ቢችሉም ደካማ ከነበረው የአጨራረስ አቅማቸው አኳያ ከጎል ጋር ሊገናኙ ግን አልቻሉም። እንዳልካቸው ፣ ኮንኮኒ እና በየነ ባንጃው ተቀይረው ገብተው ጥራት የታከለባቸውን ሙከራዎች ቢያደርጉም ሳይሳካላቸው ጨዋታ በመቻል አሸናፊነት ተቋጭቷል።


