የአራተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ የተደረጉ ሁለት መርሀግብሮች በሲዳማ ቡና እና ፋሲል ከነማ ባለ ድል አድራጊነት ተቋጭቷል።
ሲዳማ ቡና 2-0 ወላይታ ድቻ
እጅግ በርካታ ደጋፊዎች በታደሙበት እና በፌድራል ዋና ዳኛ ሔኖክ አበበ መሪነት የጀመረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ አጀማመሩ የሲዳማ ቡናን ፈጣን የማጥቃት እንቅስቃሴ እያሳየን ቀጥሎ 4ኛው ደቂቃ ላይ ግን ወላይታ ድቻዎች ተከላካያቸው ናትናኤል ናሲሩ በሜዳው የግራ መስመር አካባቢ የሲዳማ ቡናውን አጥቂ ብለስ ናጎን በክርን በመማታቱ በሁለተኛ ረዳት ዳኛው ሲራጅኑርገን ጥቆማ በቀጥታ ቀይ ካርድ ከሜዳ ሊወገድ ችሏል። ጨዋታው ቀጥሎ 10ኛው ደቂቃ ላይ እንደደረሰ ሲዳማዎች ጎልን ማስቆጠር ችለዋል። ብርሀኑ በቀለ ከቀኝ መስመር አቅጣጫ ወደ ውስጥ ያሻገረውን ኳስ ፍቅረየሱስ ተወልደብርሃን በግንባር ገጭቶ ከመረብ በማሳረፍ የሲዳማን ደጋፊዎች ያናወጠች ጎል አስቆጥሮ ቡድኑን መሪ ማድረግ ችሏል። ጨዋታው ጎል ከተቆጠረ በኋላ ይበልጥ ከፍ ያሉ ተነሳሽነቶችን ከሰላሳ ደቂቃዎች በኋላ ማሳየት የቻሉት የጦና ንቦቹ በተደጋጋሚ ወደ ጨዋታ ለመመለስ የመጨረሻው ሜዳ ላይ መዳረሻቸውን በማድረግ ብልጫውን ቢይዙም ኳስ እና መረብን ማገናኘቱ ላይ ደካሞች ነበሩ።
ከዕረፍት መልስ የጦና ንቦቹ ፈጣን ሽግግሮችን ሲዳማ ቡናዎች በበኩላቸው ጥንቃቄ ላይ ትኩረት ባደረጉበት ሁለተኛው አጋማሽ በይበልጥ ለሳጥኑ የተጠጋን እንቅስቃሴ ድቻዎች ማሳየት ቢችሉም ጨዋታው ከነበረው ሐይል የቀላቀለ አጨዋወት አኳያ እጅግ የደበዘዙ ፉክክሮች ልናስተውል ችለዋል። ብሩክ ኤልያስ ካገኛት ግልፅ አጋጣሚ ባሻገር እንደነበራቸው ብልጫ ወደ አቻነት መሸጋገር ያልቻሉት ወላይታ ድቻዎች መደበኛው ደቂቃ ተጠናቆ በተሰጠው ጭማሪ አስር ደቂቃ ውስጥ መባቻው ላይ ተቀይሮ የገባው መላኩ አሰፋ ከሳጥን ውጪ አክርሮ መቶ ጎልን በማከል በመጨረሻም ጨዋታው በሲዳማ ቡና 2ለ0 አሸናፊነት ተቋጭቷል።
- ማሰታውቂያ -

ፋሲል ከነማ 1-0 ምድረገነት ሽረ
ምሽቱን የተደረገው እና ብዙም የጎል ሙከራዎች ያልታዩበት የፋሲል ከነማ እና ምድረገነት ሽረ መርሀግብር በመጀመሪያዎቹ ሰላሳ ደቂቃዎች ውስጥ ቶሎ ቶሎ በሚጣሉ ኳሶች መጫወትን መርጠው የተስተዋሉት ፋሲሎች 34ኛው ደቂቃ ላይ ከሳጥኑ የግራ ክፍል ቃልኪዳን ዘላለም ከመረብ ያገናኛት ጎል አፄዎቹን መሪ እንዲሆኑ አድርጋለች። በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ሜዳ ላይ ከሚታዩ እንቅስቃሴዎች በስተቀር የተለየ የጨዋታ ብልጫን ቡድኖች ለመውሰድ ጥረት ሲያደርጉ አላስተዋልንም።
በሁለተኛው አጋማሽ ምድረገነት ሽረ በአንፃራዊነት የበላይነትን መያዝ የቻሉበት ቢሆንም በተለይ አጥቂዎቹ ዳንኤል ዳርጌ እና አቤል ማሙሽ የሚያገኟቸውን አጋጣሚዎች ወደ ግብነት መቀየሩ ላይ ብዙም ስኬታማ አልነበሩም። በአጋማሹ ከጨዋታው ይልቅ ትኩረት የሳበው ጨዋታው ሊጠናቀቅ ሲቃረብ ሁለት ተጫዋቾች በቀይ ካርድ ከሜዳ የተወገዱበት ነበር። 90ኛው ደቂቃ የፋሲል ከነማው የመስመር ተከላካይ ብሩክ አማኑኤል በሰራው ጥፊት በሁለት ቢጫ ካርድ በቀይ ካርድ የወጣበት እና ከሁለት ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ተቀይሮ የገባው የስሑል ሽረው አማካይ ቢኒያም ላንቃሞ ከዕለቱ የመሐል ዳኛ ቴዎድሮስ ምትኩ ጋር በፈጠረው ሰጣ ገባ በቀይ ካርድ ከሜዳ የተወገደበት እንዲሁም ጨዋታው ከተጠናቀቀ በኋላ የሁለቱም ቡድን አባላት ለጥል የተጋበዙበትን ሂደት የተመለክን ሲሆን ጨዋታው ግን በፋሲል ከነማ 1ለ0 አሸናፊነት የቋጩበት ነበር።


