በሲቢኢ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን መርሐግብር ነገሌ አርሲን በአዲስ አበባ ስታድየም የገጠመው ቅዱስ ጊዮርጊስ 1 ለ 0 አሸንፏል።
በጨዋታ እንቅስቃሴ ቅዱስ ጊዮርጊስ አንፃራዊ ብልጫ በወሰደበት የመጀመሪያ አጋማሽ ፈረሰኞቹ በተሻለ ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል መድረስ ችለዋል።
በቀኝ መስመር በኩል ባደላው የቅዱስ ጊዮርጊስ የማጥቃት እንቅስቃሴ በተለይም አቤል ያለው ጠንካራ የግብ ሙከራዎችን አድርጓል።
በ10ኛው ደቂቃ ላይ አዲሱ አቱላ ከቅጣት ምት በቀጥታ ወደ ግብ የሞከረው እና በዳዊት መለሰ ተጨርፎ ለጥቂት የወጣው እንዲሁም ፍፁም ጥላሁን ከቢንያም ፍቅሬ የደረሰውን ኳስ በግንባር ገጭቶ አስቆጠረው ሲባል ኢላማውን ያልጠበቀለት ሙከራ ቀዳሚዎች ነበሩ።
- ማሰታውቂያ -


በነገሌ አርሲ በኩል በቀላሉ የቅዱስ ጊዮርጊስን የኋላ መስመር አልፈው የግብ ዕድሎች ለመፍጠር ቢቸገሩም በአጋማሹ የመጨረሻ ደቂቃዎች ላይ ዕድሎችን መፍጠር ችለዋል።
በ38ኛው ደቂቃ ላይ የቀድሞው የቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫዋች ዳዊት ተፈራ ከሳጥን ውጪ አክርሮ የመታው ኳስ ለጥቂት ወደ ውጪ ሲወጣ ሌላኛው የቀድሞ የቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫዋች ዳግማዊ አርአያ ከቅጣት ምት ያደረገው ጠንካራ የግብ ሙከራ በኬንያዊው ግብ ጠባቂ ተመልሷል።
በ40ኛው ደቂቃ ላይ ደግሞ ቶሎሳ ንጉሴ ከመስመር ያሻረገውን ኳስ አቤል ያለው በግንባር ገጭቶ ወደ ግብ የላከው ኳስ እድሪሱ አብዱላሂ ግብ ከመሆን አድኖታል።
በሁለተኛው አጋማሽ የቅዱስ ጊዮርጊስ ሙሉ ብልጫ በነበረው ጨዋታ ፈረሰኞቹ በተደጋጋሚ የነገሌ አርሲን የኋላ ክፍል መፈተን ችለዋል።

በ53ኛው ደቂቃ ፍፁም ጥላሁን ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ ሲያደርግ በ64ኛው ደቂቃ ላይ ደግሞ አዲሱ አቱላ ከማዕዘን አሻግሮ ዳግም ያገኘውን ኳስ አክርሮ ወደ ግብ በመምታት ከባድ ሙከራ ቢያደርግም እድሪሱ አድኖታል።
ጨዋታው በቅዱስ ጊዮርጊስ ብልጫ ሲቀጥል ተደጋጋሚ ጉሽሚያዎች የነበሩበት እና የዕለቱ ዋና ዳኛ መስፍን ዳኜ ፊሽካ በተደጋጋሚ የተሰማመበት ነበር።
ጨዋታው 77ኛው ደቂቃ ላይ ሲደርስ ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለ ድል የሆነበትን ግብ አቤል ያለው የዳዊት መለሰን ስህተት በመጠቀም ከመረብ አሳርፏል።

በመጨረሻዎቸ የጨዋታው ደቂቃዎች ላይ ፍፁም ጥላሁን ያደረገው ጠንካራ የግብ ሙከራ በግብ ጠባቂው ሲመለስ ተገኑ ተሾመ ከመስመር ይዞ የገባውን ኳስ በተገቢው ቦታ ሳያደርስ ቀርቷል።
በመጨረሻም ከተጨመሩት አምስት ደቂቃዎች በኋላ የቅዱስ ጊዮርጊስ አሸናፊነት በዋና ዳኛው ፊሽካ ሲበሰር በአሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ የሚመራው ክለቡ ተከታታይ ሁለተኛ ድሉን አስመዝግቧል።
በአራተኛው ሳምንት ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሸገር ከተማ ነገሌ አርሲ ደግሞ ከባህርዳር ከተማ ይጫወታሉ።


