የሊጉ የሁለተኛ ቀን የሀዋሳ ሁለት ጨዋታዎች አፄዎቹን እና ብርቱካናማዎቹን ባለ ድል በማድረግ ተጠናቀዋል።
ወልዋሎ ዓ/ዩኒቨርስቲ 0-2 ፋሲል ከነማ
የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ስታዲየም የዕለቱ ቀዳሚ ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ ተመጣጣኝ የሚመስል እንቅስቃሴዎች ቢበራከቱም ከግብ ሙከራዎች አኳያ ግን ደብዘዝ ያለ መልክ ነበረው። ወደ መስመር ባደሉ የጨዋታ ዘይቤዎች በይበልጥ ለመንቀሳቀስ ጥረት በተደረገበት የሁለቱ ቡድኖች መርሀግብር ወልዋሎዎች በአንፃራዊነት ወደ ግብ በመድረሱ የተሻሉ ቢመስሉም ጎሎችን ሳንመለከት ወደ መልበሻ ክፍል ጨዋታው ተጉዟል።

- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ የተጫዋቾችን ቅያሪ በማድረግ ማጥቃት ላይ ትኩረት ባደረገ አጨዋወት የተመለሱት ፋሲሎች ናትናኤል ገብረጊዮርጊስ ከበረከት ግዛው ያገኘውን ሰንጣቂ ኳስ በአንድ ለአንድ ግንኙት በዩጋንዳዊው የግብ ዘብ ሙታክብዋ ጆኤል ከመነከነበት በኋላ ደቂቃው 52ኛው ላይ እንደደረሰ አምሳሉ ጥላሁን ከቀኝ መስመር አቅጣጫ የተገኘን የቅጣት ምት ሲያሻማ በግብ ዘቡ ሙታክብዋ ጆኤል ስትመለስ ኳሷን ነፃ ቦታ ሆኖ ያገኘው በረከት ግዛው ከሳጥን ውጪ አክርሮ መቶ ያሳረፋት ጎል አፄዎቹን ቀዳሚ አድርጓቸዋል።
ቢጫዎቹ በፈጣን ሽግግር አፄዎቹ በአንድ ሁለት ንክኪ በቀጣዮቹ ደቂቃዎች መርጠው ለመጫወት በሞከሯቸው እንቅስቃሴዎች ውስጥ ተጨማሪ ጎልን ያገኙት ግን ፋሲሎች ሆነዋል። 52ኛው ደቂቃ ናትናኤል ገብረጊዮርጊስ ከቀኝ ያሻማውን ኳስ የነፃነት ገብረመድኅን ስህተት ታክሎበት አቤኔዘር ዮሐንስ ሁለተኛ ጎል በማድረግ የቡድኑን የጎል መጠን ከፍ ማድረግ ችሏል። ጎሎችን ካስናገዱ በኋላ ወደ ጨዋታ ለመመለስ ወልዋሎዎች በኮንኮኒ ሀፊዝ አማካኝነት መልካም አጋጣሚን ቢያገኙም የግብ ዘቡ ሞይስ ፓዎቴ ካመከናት በቀሪዎቹ ደቂቃዎች ተጨማሪ ነገሮችን ሳንመለከት ጨዋታው በፋሲል 2ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።

ወላይታ ድቻ 0-1 ድሬዳዋ ከተማ
እጅግ ፈጣን እና ፋታ የለሽ እንቅስቃሴዎች ቶሎ ቶሎ ወደ ጎል መድረሶች የተበራከቱበት ነገር ግን ደካማ የመጨረሻው ሜዳ አጠቃቀሞችን በይበልጥ ባስተዋልንበት የመጀመሪያው አጋማሽ የቡድኖቹ ጨዋታ በድሬዳዋ በኩል አስራት ቱንጆ ከመስመር ሲያሻግር አብዲሳ ጀማል ለጥቂት ካመለጠችው ሙከራ በቀር የተለየ ነገርን እንደነበረው ከፍ ያለ ተነሳሽነት በጨዋታው ማስተዋል ያልቻልንበት ነበር።

ከመጀመሪያው አጋማሽ እንቅስቃሴ ከቆመበት የቀጠለው እና የተጫዋች ቅያሪን በማድረግ ጭምር የተመለሰው ሁለተኛው አጋማሽ የጦና ንቦቹ በረጃጅም ኳሶች ብርቱካናማዎቹ በአንፃሩ በቅብብል ሦስተኛው ሜዳ ላይ መገኘትን መርጠው ያስተዋልንበት ሲሆን በአጋማሹ የድቻን የመከላከል ስህተት ተጠቅመው አሸናፊ መሆን የቻሉት ግን የአሰልጣኝ ይታገሱ እንዳለው ቡድን ድሬዳዋ ነው። 74ኛው ደቂቃ ተቀይሮ የገባው መሐመድ ኑርናስር የሰጠውን ኳስ አብዱሰላም የሱፍ ወደ ሳጥን ሲያሻግር ከመቻል ቡድኑን የተቀላቀለው አቤል ነጋሽ በግንባር ገጭቶ መረብ ላይ አሳርፏት ጨዋታው 1ለ0 ሊጠናቀቅ ችሏል።


