የመቐለ እና መቻል ጨዋታ 2ለ2 ሲጠናቀቅ የንግድ ባንክ እና ምድረገነት ሽረ ጨዋታ ግን ያለ ጎል ተቋጭቷል።
መቐለ 70 እንደርታ 2-2 መቻል
የዕለቱ ቀዳሚ በነበረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ጎሎችን ያስመለተከን ጨዋታው ከፍ ባለ ግለት ውስጥ በተገኘበት የመጀመሪያው አጋማሽ በመጀመሪያዎቹ ሀያ ያህል ደቂቃዎች ውስጥ ነበር። በ13ኛው ደቂቃ መቐለዎች ሱለይማን ሀሚድ ከእጅ ውርወራ ያሻማውን ኳስ ኪቲካ ጀማ የግል ጥረቱን ተጠቅሞ ከቀኝ የሳጥኑ ጠርዝ ተፈጥሯዊ ባልሆነው እግሩ ጎል በማስቆጠር ቡድኑን መሪ ማድረግ ችሏል። ጎልን ካስተናገዱ በኋላ ምላሽን ለመስጠት ብዙ ደቂቃ ያልወሰደባቸው መቻሎች ከአንድ ደቂቃ በኋላ መሐመድ አበራ የሰጠውን ኳስ አብዱልከሪም ወርቁ ወደ ግብነት ለውጧት ቡድኑን ወደ አቻነት ማሸጋገር የቻለ ሲሆን ጨዋታው 19ኛው ደቂቃ ላይ ሲደርስ ደግሞ መምራት ጀምረዋል።

- ማሰታውቂያ -

የአቻነት ግቧን ከመረብ ያዋሀደው አብዱልከሪም ጣጣውን የጨረሰ ኳስን አቀብሎት ቸርነት ጉግሳ ሳይዘናጋ ሶፎኒያስ ሰይፈ መረብ ላይ በማስቀመጥ ከተመሪነት ወደ መሪነት ክለቡን አድርጓል። ጎሉን ካስቆጠሩ በኋላ መቻሎች በቸርነት እና መሐመድ አማካኝነት ያለቀላቸውን ተጨማሪ ዕድሎች ቢያገኙም በሶፎኒያስ ሠይፈ የግል ጥረት ከከሸፉ በኋላ አጋማሹ ተገባዷል።
በመጀመሪያው አጋማሽ ከተወሰደባቸው መጠነኛ ብልጫ መሻሻሎችን ይዘው ወደ ሜዳ የተመለሱት መቐለዎች በተለይ በፍፁም ዓለሙ ጥረቶች በርካታ አጋጣሚዎችን ሲፈጥሩ የታዩ ሲሆን የፍፁም ጥረት በመጨረሻም ሰምሮ ጎልን በማስቆጠር ጨዋታው በመጨረሻም 2ለ2 በሆነ አቻ ውጤት ፍፃሜውን አግኝቷል።

ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 0-0 ምድረገነት ሽረ
የምሽቱ መርሀግብር ያለ ጎል ተጠናቋል። ተመሳሳይ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴዎች በነበሩበት እና ብዙም የግብ ሙከራዎችን ያላስመለከተን የቡድኖቹ ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ ንግድ ባንኮች በብሩክ ብፁዕአምላክ የግንባር ኳስ እና የግብ ዘቡ ሪችሞንድ አዩ ባመከናት ሙከራ ቀዳሚ መሆን ቢችሉም ሽረዎች በመልሶ ማጥቃት ዳንኤል ዳርጌ ሳጥን ውስጥ ያገኛትን ያለቀላት ኳስ ወደ ላይ የሰደዳት ግን በአጋማሹ የተገኘች አስቆጪ አጋጣሚ ነበረች።

በሁለተኛው አጋማሽ መጠነኛ መዳከሞችን ይዞ የተመለሰው ጨዋታ ጥራት አልባ ዕድሎች መፈጠር ሳይችሉበት ያለ ጎል 0ለ0 ተደምድሟል ።


