የአዳማ ቆይታውን በሁለት መርሀግብር ዛሬ የጀመረው የሊጉ መርሀግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ሀድያ ሆሳዕናን በድል አስጀምሯል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 3-1 አርባምንጭ ከተማ
የአዳማ ቆይታውን በሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ የጀመረው የአስረኛው ሳምንት መርሀግብር የተሻለ አጀማመርን ማድረግ የቻሉት ንግድ ባንኮች መሪ የሆኑበትን ጎል ያገኙትን ገና በጊዜ ነበር። 5ኛው ደቂቃ ላይ ለወትሮ ስህተት በማያጣው የአርባምንጭ ተከላካዮች በሳጥን ውስጥ ጥፋት የተሰራበት አምበሉ አዲስ ግደይ የተገኘችዋን የፍፁም ቅጣት ምት ራሱ ከመረብ አሳርፎ ክለቡን መሪ አድርጓል። በተጋጣሚያቸው በብዙ ረገድ ይበለጡ የነበሩት እና ወጥነት የሌለውን እንቅስቃሴን ሲያሳዩ የተስተዋሉት አርባምንጭ ከተማዎች በአጋማሹ አንድም ጥራት ያለው ሙከራን ሳያደርጉ ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።
ከዕረፍት መልስ በቀጠለው እና አሰልጣኝ በረከትን ደሙን በቀጣዮቹ የሊጉ ጨዋታዎች ላይ ለመመልከት ወሳኝነቱ ከፍ ያለውን ቦታ የሚወስደው ሁለተኛው አጋማሽ 52ኛው ደቂቃ ላይ ቡጣቃ ሸመና ከጥሩ ቅብብል በኋላ ጎል በማስቆጠር ቡድኑን አቻ ማድረግ ቢችልም በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ግን ወደ ጨዋታው በይበልጥ በመግባት ጫናን ማሳደር የቻሉት ንግድ ባንኮች 76ኛው ደቂቃ ላይ አዲስ ግደይ የሰጠውን ኳስ ሳይመን ፒተር ከመረብ ሲያሳርፍ 88ኛው ደቂቃ ላይ ደግሞ አዲስ ግደይ ከሳይመን ፒተር ያገኘውን ኳስ ለራሱ ሁለተኛ ለቡድኑ ሦስተኛ ጎል በማድረግ ጨዋታው በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 3ለ1 አሸናፊነት ተጠናቋል።

- ማሰታውቂያ -
መቐለ 70 እንደርታ 1-2 ሀድያ ሆሳዕና
ሁለቱን የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸውን አሰልጣኞች ያገናኘው የምሽቱ መርሀግብር በቀዳሚው አጋማሽ ብልጫውን ለመውሰድ ጥረት ያደረጉት መቐለዎች እንደነበራቸው ብልጫ ጎልን 36ኛው ደቂቃ ላይ አስቆጥረዋል። ከማዕዘን ምት የተሻማች ኳስን በንክኪ ያገኘው ተከላካዩ ተመስገን ተስፋዬ ወደ ጎልነት ለውጦ የሰሜኑን ክለቡ ቀዳሚ አድርጓል። በመጀመሪያው አጋማሽ በብዙ ረገድ ኳስን መሠረት ባደረገ እንቅስቃሴ በወሰዱት ብልጫ ተጨማሪ ጎልን የማስቆጠር ዕድል የነበራቸው መቐለዎች ከዕረፍት ሲመለሱ ግን ተጋጣሚያቸው አሻሽሎ በገባው የጨዋታ መንገድ ጎሎችን ያስተናገዱበት ነበር።
ብሩክ በየነ በገጠመው ጉዳት ለተጨማሪ ህክምና ወደ ሆስፒታል ከሸኙ በኋላ የተጫዋቾች ለውጥን አድርገው በይበልጥ ወደ መስመር አጋድለው መጫወት የቻሉት ነብሮቹ 65ኛው ደቂቃ ከቅጣት ምት በተሻማ እና ተከላካዩ ቃልአብ ውብሸት እና የግቡ ቋሚ ብረትን ገጭታ የተመለሰች ኳስን ተመስገን ብርሀኑ በቀላሉ መረቡ ላይ በማስቀመጥ ቡድኑን 1ለ1 ማድረግ ችሏል። ተጨማሪ የማሸነፊያ ጎልን ለማግኘት በታታሪነት መጫወት የቻሉት ሀድያ ሆሳዕናዎች 76ኛው ደቂቃ ላይ ተመስገን ብርሀኑ እጅግ አስደናቂ ጎልን ለራሱም ለቡድኑም አክሎ ጨዋታውን ወደ 2ለ1 አሸጋግሯል። መደበኛውን የጨዋታ ደቂቃ ሊጠናቀቅ በቀረው ሰባት ደቂቃዎች ውስጥ የመቐለን ብቸኛ ጎል ያስቆጠረው ተመስገን ተስፋዬ በሰራው ጥፋት በዕለቱ ዳኛ ተፈሪ አለባቸው ሁለተኛ ቢጫ ተመዞበት በቀይ ካርድ ከሜዳ ከወጣ በኋላ ጨዋታው ተጨማሪ ጎል ሳናይበት ተቋጭቷል።


