በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት ስድስተኛ እና ሰባተኛ መርሐግብሮች ዛሬ ተደርገዋል።
በዕለቱ ቀዳሚ ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና ከፋሲል ከነማ ተገናኝተው በቡናማዎቹ የ1 ለ 0 አሸናፊነት ተጠናቋል።
ጋናዊው ኮንኮኒ ሀፍዝ በ24ኛው ደቂቃ ላይ ቡናማዎቹን አሸናፊ ያደረገውን ግብ አስቆጥሯል።
በጨዋታው 82ኛ ደቂቃ ላይ የኢትዮጵያ ቡናው ተጫዋች ረጂብ ሚፍታህ በአማኑኤል ገብረሚካኤል ላይ በሰራው ጥፋት በሁለተኛ ቢጫ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል።
- ማሰታውቂያ -
ውጤቱንም ተከትሎ ኢትዮጵያ ቡና ነጥቡን 39 በማድረስ ነገ ጨዋታውን ከሚያደርገው የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን ያለውን ልዩነት ወደ ስድስት አጥብቧል።
በደረጃ ሰንጠረዡም ትናንት ሽንፈት ያስተናገዱትን ወላይታ ድቻ እና ባህርዳር ከተማን በመብለጥ 2ኛ ላይ ተቀምጧል።
ፋሲል ከነማ በበኩሉ በ33 ነጥቦች በነበረበት 8ኛ ደረጃ ላይ ለመቆየት ተገዷል።
በ26ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና ከሲዳማ ቡና ፋሲል ከነማ ደግሞ ከድሬዳዋ ከተማ ይጫወታሉ።
የዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ ከአመሻሽ 12:00 ጀምሮ ሲደረግ ባሳለፍነው ሳምንት ከዘጠኝ ተከታታይ ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል የተመለሰው መቻል ተከታታይ ድል አስመዝግቧል።
አርባምንጭ ከተማን የገጠመው መቻል በሽመልስ በቀለ የ72ኛ ደቂቃ ግብ 1 ለ 0 አሸንፏል።
ሽመልስ በቀለ ባሳለፍነው ሳምንትም መቻል መቀሌ 70 እንደርታን ሲያሸንፍ ብቸኛውን ግብ ማስቆጠሩ ይታወሳል።
ውጤቱንም ተከትሎ መቻል ነጥቡን 35 በማድረስ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ በ34 ነጥቦች 7ኛ ደረጃ ላይ ለመቆየት ተገዷል።
በ26ኛው ሳምንት መቻል አዳማ ከተማን አርባምንጭ ከተማ ደግሞ ስሁል ሽረን ይገጥማሉ።


