የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬም ቀጥለው ሁለት ጨዋታዎች ሲደረጉ ከቀን 9:00 ጀምሮ ባህርዳር ከተማን ከፋሲል ከነማ ያገናኘው የደርቢ ጨዋታ ያለ ግብ ተጠናቋል።
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ ባህርዳር ከተማዎች የተሻለ የተንቀሳቀሱበት እና የግብ ዕድሎች በመፍጠርም የበላይ የሆኑበት ቢሆንም ጥረቶቻቸው ኳስና መረብን ማገናኘት የቻሉ አልነበሩም።
በሁለተኛው አጋማሽ ከቀዳሚው አጋማሽ ተሽለው የቀረቡት ፋሲል ከነማዎች የሜዳ ላይ እንቅስቃሴያቸው በሙከራዎች የታጀበ አልነበረም።
ለመጀመሪያ ጊዜ በቡድኑ የመጀመሪያ አሰላለፍ ተካቶ የተጫወተው ቢንያም ጌታቸው በ57ኛው ደቂቃ ላይ የግብ አካውንቱን መክፈት የሚችልበትን የፍፁም ቅጣት አግኝቶ ሳይጠቀምበት ቀርቷል።
- ማሰታውቂያ -
በርካታ የአቻ ውጤቶችን የሚያስመለከተን የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ዛሬ ለ12ኛ ጊዜ ሲደረግ 8ኛ የአቻ ውጤትንም አስመዝግቧል።
ውጤቱንም ተከትሎ ባህርዳር ከተማ ነጥቡን 30 በማድረስ ወደ 4ኛ ደረጃ ከፍ ሲል ፋሲል ከነማ በበኩሉ በ24 ነጥቦች በነበረበት 12ኛ ደረጃ ለመቆየት ተገዷል።
በ22ኛ ሳምንት መርሐግብር ባህርዳር ከተማ ከሀድያ ሆሳዕና እንዲሁም ፋሲል ከነማ ከመቻል ይገናኛሉ።
የዕለቱ ሁለተኛ መርሐግብር ደግሞ ከአመሻሽ 12:00 ጀምሮ ሲደረግ ወላይታ ድቻዎችን ለተከታታይ ደስታ ቅዱስ ጊዮርጊሶችን ደግሞ ለተከታታይ ብስጭት የዳረገ ውጤት አስመዝግቧል።
እምብዛም ጠንካራ የግብ ሙከራዎች ያልነበሩት ጨዋታው በ58ኛው ደቂቃ ላይ ብቸኛውን ግብ አስተናግዷል።
በተጠቀሰው ደቂቃ ላይ ቴዎድሮስ ታፈሰ ከቆመ ኳስ ያሻገረውን ኳስ አብነት ደምሴ በግንባር በመግጨት መረብ ላይ አሳርፎታል።
ወላይታ ድቻ ባሳለፍነው ሳምንትም ኢትዮጵያ መድንን በፀጋዬ አበራ ብቸኛ ግብ በተመሳሳይ 1 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው።
ቅዱስ ጊዮርጊስ በበኩሉ በሀድያ ሆሳዕና እና በባህርዳር ከተማ ከተሸነፈባቸው ጨዋታዎች በኋላ ሶስተኛ ተከታታይ የሊግ ሽንፈትን አስመዝግቧል።
ውጤቱን ተከትሎ ወላይታ ድቻ ነጥቡን 30 ያደረሰ ሶስተኛው ክለብ በመሆን የ5ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በበኩሉ በነበረው 29 ነጥብ ወደ 7ኛ ደረጃ ዝቅ ብሏል።
በመጪው ዕሁድ በሚጀምረው የ22ኛ ሳምንት መርሐግብር ወላይታ ድቻ ከወልዋሎ አዲግራት እንዲሁም ቅዱስ ጊዮርጊስ ከድሬዳዋ ከተማ ይጫወታሉ።


