ፈጣኑ የፊት አጥቂ መሀመድ ኑር በጅፋርያውያን መንደር ለመንገስ መስማማቱ ተነገረ።
በመድን ድርጅት የአንድ አመት ኮንትራት ቢኖረውም በፕሪሚየር ሊጉ ክለቦች በመፈለጉ ጀርባውን ለመድን የሰጠው መሃመድ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ለመፈረም የነበረው እድል በአዲሱ ሰርቪያዊ አሰልጣኝ እንቢተኝነት አለመሳካቱ ከተነገረ ቀናቶች በኋላ ለጅማ አባጅፋር የመጫወት እድል አግኝቷል። ኢትዮጵያ ቡና ተጨዋቹን ለማስፈረም እድል ቢኖረውም ፈጣን ነው ከኛ አጨዋወት ጋር አይሄድም በሚል ሳይፈርም ቀርቷል። ያም ሆኖ የቀድሞ የቅዱስ ጊዮርጊስ የአሁኑ የጅማ አባጅፋር የፊት መስመር ተዋጊ ሳላህዲን ሰይድ በሰጠው ጥቆማና አሰልጣኙም እምነት በመጣሉ
ለጅማ አባጅፋር የመፈረም እድል አግኝቷል።
ተጨዋቹ ፍጥነቱና ግብ የማስቆጠር አቅሙ ታክሎበት በአሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ስር በመሃል ሜዳ ኮከቦቹ ዳዊት እስጢፋኖስና መስዑድ መሃመድ በርካታ ግብ የማስቆጠር እድል ፈጠራ ታግዞ በ2014 በጅማ አባጅፋር ብሎም በሊጉ ውጤታማ ጊዜ ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል።
የመድን አመራሮች ለዝውውር የጠየቁትን 500ሺህ ብር ጅማ አባጅፋሮች ለመክፈል የተስማሙ ሲሆን ክለቡ ከኤጀንቱ ጋር ጋር ከተደራደረ በኋላ ለተጨዋቹ እስከ 100ሺህ ብር ደመወዝ ለመክፈል መስማማቱ ታውቋል።
ከዚህ ቀደም ተጨዋቹ በወዳጅነት ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 የረታበትን ግብ አስቆጥሮም ቢሆን የአሰልጣኙን ይሁንታ አለማግኘቱ የገረመው አልሆነም።
ከትላንት በስቲያ ረቡእ ጅማ አባጅፋር የደብረዘይት ወጣቶችን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ የአንዱ ግብ ባለቤት ሲሆን ለማንኛውም ቡድን ግብ የማስቆጠር ብቃት እንዳለው አስመስክሯል።
አስተያየት ይስጡ