በቤት ኪንግ ፕሪምየር ሊጉ ሰበታ ከተማ በስኳዱ ከያዛቸው ወጣት ተጨዋቾቾ መካከል አንዱ የሆነው እና ለክለቡም ጥሩ ሲንቀሳቀስ የተመለከትነው ፉዐድ ፈረጃ ከሀትሪክ ስፖርት ድረ-ገፅ ጋር አጠር ያለ ቆይታን አድርጓል።
ስለ ኳስ ጅማሬው እና ስለ ተቀዳጀው ድል
“የእግር ኳስን መጫወት የጀመርኩት በተወለድኩበት የአዳማ ከተማ ውስጥ ነው።
ገና ታዳጊ ሆኜም ነበር ክለቡን የተቀላቀልኩት። በ2008 ላይም የተስፋው ቡድን ተጨዋች ነበርኩ። በዚህ ቡድን ቆይታዬም ቅዱስ ጊዮርጊስን በማሸነፍ ድልን ልቀዳጅም ችያለው። ከ2009 ጀምሮም እስከ አምና ድረስ የዋናው ቡድን ተጨዋች ሆኜ ቆይቻለው”።
- ማሰታውቂያ -
በልጅነት እድሜው አርአያ ስላደረገው ተጨዋች
“የእግር ኳስን ከልጅነቴ እድሜዬ ጀምሮ ስጫወት አድንቄያቸው ያደግኩት ተጨዋቾች ብዙ ቢኖሩም እንደ አዲስ ህንፃ የሚሆንብኝ ተጨዋች ግን ማንም የለም። ወላጅ አባቴም ነበር ያኔ በአዳማው የአበበ ቢቂላ ስታድየም ኳስን እንድመለከት ይዞኝ በሚገባ ሰዓት ላይም በዚህ ተጨዋች ችሎታ ተማርኬ ተምሳሌቴ ላደርገው የቻልኩት”።
ስለ ወቅታዊ ብቃቱ
“ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ለቡድኔ በጉዳት ባልጫወትም ዘንድሮ በጥሩ ብቃቴ ላይ ነው የምገኘው። ገና ወጣት ተጨዋች ነኝ። ይሄንን ጥሩ እና አበረታች የሚባለውን ችሎታዬንም ከዚህ በበለጠም ደረጃ ላይ ለማስቀጠል አሁንም እየተዘጋጀው ነው”።
በቤት ኪንግ ፕሪምየር ሊጉ ቡድናቸው እያደረገ ስላለው ጉዞ
“ውድድሩን ስንጀምር በኳሱ ደረጃ ጥሩ ስንንቀሳቀስ ነበር። ጥሩም የተጨዋቾች ስብስብም ነው ያለን። በፋሲሊቲ ደረጃ ሲኬድ ግን የአንድ አንድ ነገሮች አለመሟላት በውጤት ረገድ የምንፈልገውን ያህል እንዳናመጣ ነው ያደረገን። የሁለተኛው ዙር ላይ ግን ቡድናችን ሌሎች ያሉበትንም ክፍተቶች ቀርፎ ውጤታማነቱን እንደሚያሳይ እርግጠኛ ነኝ”።
በቤት ኪንግ ፕሪምየር ሊጉ ውጤትን ስላሳጣቸው ሌሎች ችግሮቻቸው
“በዚህ ዙሪያ ከምጠቅሰው ውስጥ የአሰልጣኙን የኳስ ፍልስፍና በፍጥነት ካለመተግበር ጋር ተያይዞ በራሳችን ላይ አደጋ እንዲፈጠር ያደረግንበትና በአንድ አንድ ጨዋታዎች ላይ ደግሞ የዳኞችም ችግሮች ስለነበሩ እነዚህ ሊጎዱን ችለዋል። ከዚህ በኋላ ግን አሰልጣኛችን የሚሰጠንን እያንዳንዱን መመሪያ እና ትህዛዝ ወደ ተግባር በመቀየር ወደ ጥሩነታችን የምንመለስ ይሆናል”።
ስለ ቀጣይ ጊዜ እቅዱ
“የሊግ ዋንጫን ማንሳት እና ለብሄራዊ ቡድን ተመርጦ መጫወትን እፈልጋለሁ። በኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ ትላልቅ ቡድኖች ውስጥም ገብቼ የመጫወቱ ትልቅ እልሙም አለኝ።
ፕሮፌሽናል ተጨዋች መሆንም የመጨረሻው ግቤ ነው”።
የቤት ኪንግ ፕሪምየር ሊግ ምርጡ ተጨዋች
“ምርጡ ተጨዋች ለእኔ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ሊሆን የሚገባው የኢትዮጵያ ቡናው አቡበከር ናስር ነው”።
በመጨረሻ
“ቤተሰቦቼ በተለይ ደግሞ አባቴ ኳስ ተጨዋች እንድሆን በብዙ ነገር አግዞኛል። ከፈጣሪዬ በኋላም እሱንና ሌሎችን አመሰግናችኋለሁ “።