በዮሴፍ ከፈለኝ
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዋንጫን በማንሳት ከክልል ክለቦች ቀዳሚው ነው ጠንካራ ተፎካካሪ በመሆንም ይታወቃል… ሀዋሳ ከተማ፡፡ የ2013 የሊጉ መርሃ ግብር ላይ 2 ጨዋታዎች ተረትቶ ያለምንም ነጥብ ከታች የሚገኘው ሀዋሳ ከተማ ከ13 ክለቦች ሶስቱ በሚወርዱበት ሂደት ወራጅ ይሆን እንዴ የሚለው ስጋት የብዙዎች ቢሆንም ከሀትሪኩ ዮሴፍ ከፈለኝ ጋር ቆይታ ያደርገው የክለቡ ዋና አሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረት ግን የመውረድ ስጋት በፍፁም የለብንም ሲል መልሷል፡፡ አሰልጣኝ ሙሉጌታ ከሀትሪክ ለቀረቡለት ጥያቄዎችም የሰጠው ምላሽ ይህን ይመስላል፡፡
ሀትሪክ፡- ከቀድሞው የዋሊያዎቹ አሰልጣኝ አብርሃም መብራቱ ጋር የነበረህን ቆይታ እንዴት ታየዋለህ?
ሙሉጌታ፡- ከአሰልጣኝ አብርሃም መብራቱ ጋር የሰራሁበት ጊዜ ለኔ ምርጡ ጊዜ ነበር፡፡ ከጠበኩት በላይ የተደሰትኩበትም ጊዜ ነው፤ ሀዋሳ ከተማ እያለሁም ከአሰልጣኝ ውበቱ አባተ ጋር ሠርቻለሁ የተሻለ እውቀትና ትምህርት አግኝቼ ነው ሀዋሳ ከተማን የተረከብከት…. በተለይ ከአሠልጣኝ አብርሃም ጋር የነበረኝ ጊዜ ለኔ በራስ መተማመኔን ጨምሮልኛል፡፡
- ማሰታውቂያ -
ሀትሪክ፡- ሀዋሳ ከተማን በተጨዋችነትም በአሰልጣኝነትም ማገልገል ምን ስሜት ይፈጥራል?
ሙሉጌታ፡- ተጫውቼ ያሳለፈኩበትን ክለብን ማሰልጠን ትልቅ ደስታ ይፈጥራል አጋጣሚው መፍጠኑ ደግሞ የተለየ ያደርገዋል የተወለድኩበት ከተማና ያደኩበት ክለብ መሆኑ ያስደስታል… እንደመጀመሪያ ከሌላ ክለብ ይልቅ በሀዋሳ መጀመሬ ለኔ ትልቅ እድል ነው፡፡
ሀትሪክ፡-በሊጉ ጅማሬ 2 ጨዋታ በተከታታይ የመሸነፋችሁ ምክንያት ምን ይሆን?
ሙሉጌታ፡- ምንም የተለየ ነገር የለውም የዘንድሮ የፕሪማየር ሊግ ውድድር ትንሽ ጠንከር ያለ ይመስላል ቡድናችን ውስጥ በርከት ያሉ ወጣቶች እንደመኖራቸው ከተወሰኑ ሲኒየር ተጨዋቾች ጋር አቀናጅተን ወደ ውድድር ብንገባም ዘግየት ማለታችን አስቸግሮናል፡፡ አየሩና የተዘጋጀንበት ሜዳ ሊስተካከልልን አልቻለም የጥቂት ተጨዋቾች ጉዳት ወጥ የሆነ አቋም እንዳናሳይ አድርጎናል፡፡ የአዲስ አበባ አየርና ሜዳው ውጤት ላይ ተፈታትኖናል፡፡ ከጨዋታ ጨዋታ ግን ተከተካክለን የተሻለ አቋም እናሳያለን ብዬ አስባለው፡፡
ሀትሪክ፡-በወጣቶች የተሞላ ቡድን መሆኑ ጥሩ ነው ነገር ግን ፊት ላይ የአጨራረስ ድክመት የሚታይ ይመስላል ይህን ታዝበሃል?
ሙሉጌታ፡-ትክክል ነው ይህ ክፍተት ታይቶብናል፡፡ ተጨዋቾቼ ሜዳውና አየሩን ሲለምዱትና የተጎዱት ሲመለሱ ወደ ውጤታማነት እንመለሳለን ብዬ አምናለሁ አንድ ልምድ ያለው አጥቂንም ብናገኝ ጥሩ ነበር፤ አልተሳካልንም እስራኤል እሸቱ የተሰኘው አጥቂ እኛ ጋር ፈርሞ ቆየና ባለቀ ሰዓት ወደ ሌላ ክለብ ማምራቱ ጎድቶናል ቀድመን ብናውቅ የተሻለ አጥቂ እናስፈርም ነበር.. ነገር ግን ተጨዋቹ የለቀቀው ባለቀ ሰዓት በመሆኑ አልተሳካልንም ያም ቢሆን አሁን ባሉት ወጣቶች ክፍተቶችን እያጠጋገንን 1ኛ ዙርን ለመጨረስ እንሞክራለን፡፡
ሀትሪክ፡-አሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረት ስራውን የሚሰራው በጫና? ወይስ ዘና ብሎ?
ሙሉጌታ፡-/ሳቅ/ ኧረ ዘና ብሎ ነው ገና ውድድሩ ሳይጀመር የምን ጫና ይኖራል?
ሀትሪክ፡- ከግጥሚያው ጀርባ ያለ ፍትጊያ የለም እያልክ ነው? ቦታውን የሚፈልጉ ሰዎች ጫና ውስጥ ከተውሃል ይባላል ስህተት ነው?
ሙሉጌታ፡-ይህን አላውቅም ነገር ግን ስራ ስትሰራ የሚወድህም የሚጠላህም ይኖራል ይህን አይነት ቻሌንጅ ዛሬ ብቻ ሳይሆን ስጫወትም የነበረ ነው ግን እነዚህ ነገሮች ቢፈጠሩ በሚል ራሴን አዘጋጅቼ ነው የመጣሁት ከሜዳ ውጪ ያለውን ጫና ካልተቋቋምክ ደግሞ ማሰልጠን ይከብዳል ምናልባት ሽንፈት ሲመጣ ጫናው ሊመጣ ይችላልና ነገር ግን በቡድኑ እምነት ስላለኝ የተሻለ ቦታ ላይ እንቀመጣለን ብዬ አስባለሁ፡፡
ሀትሪክ፡-ሀዋሳ ካፈራቻቸው ባለሙያዎች ተጫውተው ባቆሙ ድጋፍ ይደረግልሃል?
ሙሉጌታ፡- /ሳቅ/ በህብረተሰቡ ደረጃ ሙሉ ድጋፍ አለኝ የቡድኑ አሰልጣኞች ተጫውተን ያለፍን እንደመሆናችን በርቱ የሚለን ህዝብ ብዙ ነው ነገር ግን እንደባለሙያ ግን ብዙም አይደለም ባለሙያ የምትላቸውም እኛጋር ብዙም አይደሉም፤ ከጥቂቶቹ መሀል እነ ጋሽ ከማል እነ ዘላለም ሽፈራው /ሞውሪንሆ/ ከነሱ ጋር መገናኘቱ ጠባብ በመሆኑ ተገናኝተን አውርተን አናውቅም፤ ተጫውተው ካቆሙ መሃል የሚቀርቡኝ አሉ ጥሩ ምላሽም አላቸው ነገር ግን ሌሎች ችግሮች ካሉ አላውቅም እገዛው ግን ባለህ ግንኙነት የሚወሰን ይመስለኛል ሁሌ በእኔ በኩል ትኩረቴ ስራ ላይ ብቻ መሆኑን ነው የማውቀው፡፡
ሀትሪክ፡- በደመወዝና ማበረታቻ መዘግየትስ የተፈጠረ ችግር የለም?
ሙሉጌታ፡- በርግጥ ስፖርትኛ ላይ ትልቅ ተፅዕኖ የሚፈጥረው ይሄ ነው ከኛ ጊዜም ጀምሮ ቡድኖችን የሚጎዳ ነገር ከተባለ ከጥቅማ ጥቅምና ደመወዝ ጋር የተያያዘ ግጭት ነው የኛ ክለብ ግን በክፍያ አይታማም በተለይ ደግሞ ደመወዝ በጊዜ በመክፈልና ማበረታቻ በመስጠት አይታማም የተፈጠረ ክፍተትም የለም ጥሩ አካሄድ ላይ እንገኛለን፡፡
ሀትሪክ፡- ከ13 ክለቦች 3ቱ ይወርዳሉ ፉክክሩ ከባድ እንደመሆኑ አያሰጋችሁም?
ሙሉጌታ፡-በርግጥ የዘንድር የሊግ ውድድር ከብዷል ሶስት ክለቦች ወራጅ መሆናቸው በራሱ ይከብዳል እኛን ግን የሚያሳስበን ነገር ያለ አይመስለኝም፤ ጠንካራ ስምና ጠንካራ ቡድን ያለው ክለብ እንደመሆኑ አሁን የታየው ሽንፈት ከ3 እና 4 ጨዋታዎች በኋላ አይኖርም ራሳችንን ፈትሸን ሊጉ ላይ ጠንክረን እንደምንገኝ ርግጠኛ ነኝ… ወጥ የሆነ አቋማችንን ማሳየታችን አይቀርም፡፡
ሀትሪክ፡- የ2013 የአሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረትና ቡድኑ ግብ ምንድነው?
ሙሉጌታ፡- ያለን ግብ ቡድናችን በየደረጃው እየተጓዝን ጠንካራ ቡድን የመገንባት እቅድ አለን፡፡ ክለባችን የሊጉን ዋንጫ በማንሣት ይታወቃል፡፡ ደረጃ ውስጥ የማይጠፋ ክለብ ነው አሁን ደግሞ ጠንካራ ቡድን እየገነባን ከጊዜያት በኋላ የዋንጫ ተፎካካሪና ደረጃ ውሰጥ የሚቆይ ቡድን ለመፍጠር አቅደናል፡፡
ሀትሪክ፡- የመጨረሻ ጥያቄ… በ2013 የሀዋሳ ከተማ ቡድን የመውረድ ስጋት የለበትም ማለት ይቻላል?
ሙሉጌታ፡- በፍፁም የመውረድ ስጋት የለብንም በውስጣችን ርግጠኞች ጠንካራውን ሀዋሳ ከተማ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ይታያል እንጂ የመውረድ ስጋት በፍፁም አይታሰብም…፡፡