የፋሲል ከነማ ደጋፊዎች መልስ የሚያገኙበት እና ለውጦች የሚኖሩት ጠቅላላ ጉባኤ ዕሁድ ይከናወናል።
ወደ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ በማደግ በአጭር ጊዜ ውስጥ ጠንካራ ተፎካካሪ ከሆኑ ክለቦች ውስጥ መመደብ የቻለው እና የሊጉን ዋንጫም አንድ ጊዜ በማንሳት ስሙን በድል ዝርዝር ውስጥ ያስቀመጠው ፋሲል ከነማ ረዘም ካሉ አመታቶች በኋላ በተደጋጋሚ ጥያቄ ሲነሳበት የነበረውን ጠቅላላ ጉባኤ የፊታችን ዕሁድ መጋቢት 13 ሊያከናውን መዘጋጀቱን የሀትሪክ ስፖርት መረጃ አመላክቷል።
የክለቡ ደጋፊዎች ክለቡ እየገጠመው ከመጣው የውጤት ማሽቆልቆል እንዲሁም ከተፎካካሪነት እየደበዘዘ መምጣቱን ተከትሎ በተደጋጋሚ ለውጦች እንዲመጡ በየአመቱ ተቃውሞን በማሰማት ፣ የአመራር ለውጥም ይደረግ እያሉ ድምፃቸውን ሲያሰሙ የነበረ ሲሆን በጎንደር ከተማ ከንቲባ እና የክለቡ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ቻላቸው ዳኛው መልካም ፍቃድም በርካታ ጉዳዮች በሚነሱበት እና አዳዲስ ውሳኔዎች በሚወሰኑበት ጠቅላላ ጉባኤ የደጋፊው ተደጋጋሚ ቅሬታ ሊፈታ መሆኑን ጭምር በመረጃዎቻችን አረጋግጠናል። በጠቅላላ ጉባኤውም ክለቡ ዘለግ ላሉ አመታት ስራ አስኪያጅ ሆነው ክለቡን የመሩት እና ተደጋጋሚ ተቃውሞን ሲያስተናግዱ የሚታዩት አቶ አብዮት ብርሀኑን ጨምሮ እንዲሁም ክለቡን ለቀጣዮቹ አምስት አመታት በቦርድ አመራርነት የሚመሩ አካላትን የመምረጥ ሂደትም ጉባኤው እንደሚኖረውም ለማወቅ ችለናል።
አስተያየት ይስጡ