ኢትዮጲያ ቡና ካለበት የፋይናንስ ቀዉስ ለማዉጣት ከቡናዉ ሴክተር የሚገኘዉ ገንዘብ መጨመር አለበት ተባለ።
ኢትዮጲያ ቡና ስፖርት ክለብ ከረጅም አመታት ቆይታ በኋላ ዛሬ በቡና እና ሻይ መሰብሰቢያ አዳራሽ ስምንተኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤዉን አካሂዷል። በጉባኤዉ በተለይም ክለቡ አሁን ካለበት ችግር በሚወጣበት እና በቀጣይ ስትራቴጂክ ዕቅድ ጉዳዮች ላይ ጉባኤተኛዉ ሰፊ ምክክር አካሂዷል።
በዋናነት አሁን ላይ ስፖርት ክለቡ የፋይናንስ ቀዉስ ዉስጥ የሚገኝ ሲሆን ከዚህ ቀዉስ በፍጥነት ለመዉጣት ደግሞ የቡናዉ ሴክተር ለክለቡ የሚደጉመዉ ገንዘብ በእጅጉ ማሻሻል እንዳለበት ጉባኤተኛዉ አንስቷል።
የቡናዉ ሴክተር ለክለቡ ከ14 አመት በፊት በ2004 በቶን ሰላሳ ብር ለክለቡ ገቢ ሲያደርግ ቢቆይም አሁን ላይ ካለዉ የዋጋ ጭማሪ ጋር በተያያዘ ይህን ያክል አመት ሁሉ ለክለቡ የሚደጎመዉ ገንዘብ አለመጨመሩ ያለዉን ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበ እንደሆነ ተነስቷል።
ከቡናዉ ሴክተር የሚገኘዉ ገንዘብ የሚጨምር ከሆነ ኢትዮጲያ ቡና በቀጣይ የፋይናንስ ጥያቄ የማይነሳበት ክለብ ማድረግ ይቻላልም ተብሏል።
ጭማሬዉ እስካሁን ሳይደረግ መቆየቱ ልክ እንዳልሆነ የተረዳዉ የቡና እና ሻይ ተወካይ ችግሩን በመረዳት ከቡና ላኪዎች ማህበር ጋር በመነጋገር በአፋጣኝ ጭማሪ እንደሚደረግ ያላቸዉን እምነት ገልፀዋል።
አስተያየት ይስጡ