ወላይታ ድቻ የሊጉን መሪ ሲዳማ ቡናን ሲረታ ሸገር ከተማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክም ተጋጣሚዎቻቸውን ረተዋል።
መቻልን ከወልዋሎ ያገናኘው ቀዳሚው የዕለቱ ጨዋታ ያለ ጎል የተደመደመ ሆኗል። ዝግ እያሉ እንቅስቃሴዎች በበረከቱበት እና መቻሎች የተሻሉ የማጥቃት ሂደቶችን ማየት ያስቻሉበት ነበር። ከመጀመሪያው በብዙ ረገድ ተሽሎ በታየው ሁለተኛው አጋማሽ መቻሎች በይበልጥ ለጎል የተጠጉ ቢመስሉም ኳስን ከመብ ማገናኘት አልቻሉም በተለይ 76ኛው ደቂቃ ከግራ የሜዳው ሳጥን ውስጥ የወልዋሎው ተከላካይ ኪም ላም አብዱልከሪም ወርቁ ላይ በሰራው ጥፋት የዕለቱ ዋና ዳኛ ሔኖክ አበበ የሰጡትን የፍፁም ቅጣት ምት ቸርነት ጉግሳ መቶ የግብ ዘቡ ሙክታብዋ ጆኤል መልሶበት ጨዋታው በመጨረሻም 0ለ0 ተቋጭቷል።
ወላይታ ድቻ የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ላይ ሦስት ጎሎች አስቆጥሮ በመርታት ከወራጅ ቀጠናው የወጣበትን ዕድል አስመዝግቧል። ድቻዎች ከፍ ባለ አቀራረብ ሜዳ ላይ ሲንቀሳቀሱ ባስተዋልበት ጨዋታ 28ኛው ደቂቃ ላይ የመሪነት ግባቸውን አግኝተዋል። በጨዋታው የተሻለ ጊዜን ያሳለፈው አማካዩ ሙሉቀን አዲሱ በረጅሙ ያሻገረለትን ኳስ ዩጋንዳዊው የግብ ዘብ ኢማኑኤል ካል ኳሷን ለማግኘት ሲወጣ ቀድሞ ያገኛት ኪዳኔ አሠፋ በግንባሩ መረቡ ላይ አሳርፏታል። ከሁለት ደቂቃዎች መልስ ደግሞ ከማዕዘን የተሻማች ኳስን የሲዳማ ቡናው ግብ ጠባቂ ኢማኑኤል ካል ነክቶ ለማውጣት ጥረት ያደረጋት ኳስን ሙሉቀን አዲሱ ወደ ሳጥን መልሶ አሻምቶ መልካሙ ቦጋለ ዘሎ በመግጨት ሁለተኛ ጎልን አክሏል።
67ኛው ደቂቃ ጨዋታው እንደደረሰም ሦስተኛውን ጎል የጦና ንቦቹ ወደ ቋታቸው ከተዋል። ከአዲሱ ፈራሚ ሳሊፉ ኢብራሂም የተቀበለውን ኳስ ተቀይሮ ወደ ሜዳ የገባው ያሬድ ዳርዛ ተፈጥሯዊ ባልሆነው የግራ እግሩ እጅግ አስደናቂ ጎልን በሚገርም መልኩ ማስቆጠር ችሏል። 80ኛው ደቂቃ ሲዳማ ቡናዎች እያሱ ሮንዳ በረጅሙ ወደ ድቻ ሳጥን የደረሰን ኳስ በመቆጣጠር ለአዲሱ ፈራሚው አቤል ያለው ሰጥቶት ተቀይሮ የገባውም አጥቂ ቡድኑን ከሽንፈት ያላዳናች ጎል ቢያደርጋትም ጨዋታው በመጨረሻም 3ለ1 በሆነ ውጤት በጦና ንቦቹ የበላይነት ተጠናቋል።
ሀዋሳ ላይ ሸገር ከተማን ከቅዱስ ጊዮርጊስ ያፋለመው የዘጠኝ ሰዓት መርሀግብር በብዙ ፈተናዎች ውስጥ እየተጓዘ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ 1ለ0 በሆነ ውጤት ተሸንፏል። ተመጣጣኝ የሚባል ፉክክርን ሜዳ ላይ ባየንበት የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ 53ኛው ደቂቃ ገዛኸኝ ደሳለኝ ከራሱ ሜዳ በረጅሙ የላከለትን ኳስ ቢኒያም ፍቅሬ ከተከላካይ መሐል ሾልኮ በማምለጥ የቀድሞው ክለቡ ላይ ግብ አስቆጥሮ ሸገርን 1ለ0 አሸናፊ አድርጓል።
አመሻሹን ጥሩ ፉክክር የታየበት የኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ኢትዮጵያ ቡና ጨዋታ ኤሌክትሪክ 2ለ1 አሸንፎ ወጥቷል። ኤሌክትሪኮች የበላይ መሆን በቻሉበት የመጀመሪያው አጋማሽ 14ኛው ደቂቃ ላይ ከሀሰን ሁሴን ከሳጥኑ የግራ ክፍል በአግባቡ ኳስን የተቀበለው ኳስ ወጣቱ የግራ መስመር ተከላካይ ናትናኤል ዱባለ ከጠባብ ቦታ ዳላንድ ኢብራሂም መረብ ላይ የኤሌክትሪክን ቀዳሚ ጎል አስቆጥሯል።
ከዕረፍት መልስ ጨዋታው እንደተጀመረ ኤሌክትሪኮች ፈጣን ጎል አስቆጥረዋል ከእጅ ውርወራ ሀብታሙ ሸዋለም ሰንጥቆ ያቀበለውን የቡናማዎቹ ተከላካዮች ስህተት ታክሎ ጨዋታው ወደ 2ለ1 ተሸጋግሯል። ወደ መጨረሻዎቹ ሀያ አምስት ደቂቃዎች ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረት ማድረግ የጀመሩት ኢትዮጵያ ቡናዎች 60ኛው ደቂቃ ላይ ከቢኒያም ጌታቸው ያገኛችን ኳስ ወጣቱ ሀምዛ ሱልጣን ቢያስቆጥርም ቡድኑን ከሽንፈት መታደግ ሳይችል ቀርቷል።
አስተያየት ይስጡ