*…መቻልና ሲዳማ ቡና ከነተጨዋቾቻቸው በመደበኛ ፍርድ ቤት ክስ መስርተዋል….
*… የተጨዋቾቹ ቅጣት የመክፈያ የመጨረሻ ቀነ ገደብ በቀጣዩ ማክሰኞ የሚጠናቀቅ በመሆኑ ውሳኔውን ያልተገበሩ ተጨዋቾች ለየክለቦቻቸው መጫወት እንደማይችሉ ፕሪሚየር ሊጉ ትዕዛዝ ሰጥቷል…
በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ይግባኝ ሰሚ ኮሚቴ ውሳኔ ቅር የተሰኙት ሁለት ክለቦችና ተጨዋቾቻቸው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበሩን ከሰሱ።
ከታማኝ ምንጭ በተገኘ መረጃ መቻልና ሲዳማ ቡና ከነተጨዋቾቻቸው ጉዳዩን ወደመደበኛ ፍርድ ቤት በመውሰድ ፕሪሚየር ሊጉን ከሰዋል። በዚህም ለሚያዚያ 2፣14፣16 እና 21 ለሊግ ኩባንያው የፍርድ ቤት መጥሪያ ደርሶት ዓርብ ዕለት መጥሪያውን መቀበሉንም ሊግ ኩባንያው አረጋግጧል።
- ማሰታውቂያ -
ፕሪሚር ሊጉ ደንብና መመሪያውን ጥሰዋል ባላቸው ክለቦችና ተጨዋቾች ላይ ከፍተኛ የተባለ የገንዘብ ቅጣት በማስተላለፉ ለፌዴሬሽኑ ይግባኝ ሰሚ ኮሚቴ ይግባኝ ቢሉም ኮሚቴው የተላለፈው ውሳኔ ትክክል ነው ብሎ ማጽናቱ ይታወሳል።
የክለቦቹንና የተጨዋችቹን የክስ ሂደት የያዙት ጠበቃና የህግ አማካሪ ወደሆኑት አቶ ብርሃኑ በጋሻው የግል ስልክ ላይ በተደጋጋሚ ጊዜ ደውለን ምላሽ ባይሰጡንም በቀጣይ ስናገኛቸው ግን ሙሉ የክስ ሂደቱነ አጠናክረን የምንገልጽ ይሆናል።
በተመሳሳይ ዜና ቅጣት የተላለፈባቸው ተጨዋቾች በሙሉ የወሰዱትን ብር እንዲመልሱና 200ሺህ የቅጣት ብር እንዲከፍሉ የተሰጣቸው የሰባት ቀናት ገደብ የፊታችን ማክሰኞ ይጠናቀቃል።
በመሆኑም ተጨዋቾቹ ውሳኔውን እስከ ማክሰኞ ድረስ ተግባራዊ ካላደረጉ ከፊታቸን ረቡዕ ሚያዚያ 3/2017 ጀምሮ ውሳኔውን ያልተገበሩ ተጨዋችች መሰለፍ እንደማይችሉ ለውድድር ክፍል ትዕዛዝ መሰጠቱ የደረሰን መረጃ ያስረዳል።


