በዛሬው መግለጫ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ባህሩ ጥላሁን ከአስተዳደራዊ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ነጥቦችን አንስተዋል።
የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ ጅራ ከሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጋር ባላቸው ጥሩ ግንኙነት አማካይነት ብሔራዊ ቡድኑ ጨዋታዎቹን ሲያደርግ ከአውሮፕላን ጉዞ ውጪ ያሉ ወጪዎች በሙሉ በሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን እንደሚሸፈኑ ገልፀዋል።
በፌዴሬሽኑ የተሸፈነውን ወጪ የገንዘብ መጠንም ዋና ስራ አስፈፃሚው በመግለጫው ገልፀዋል።
“የሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሆቴል ፣ የትራስፖርት(ሞሮኮ ላይ) ፣ ዳኞች የሚያርፉበት እና ለነሱ የሚመደበው መኪና ከዛ በተጨማሪም ደግሞ ለግብፅ እና ለጅቡቲ ብሔራዊ ቡድኖች የሚመደቡ መኪናዎች እና የፋሲሊቲ ወጪዎች ይኖራሉ እና ከ40 እስከ 50 ሺህ ዶላር የሚሆን ወጪ የሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሚሸፍንልን ይሆናል።”
- ማሰታውቂያ -
አቶ ባህሩ አክለውም ገና የምድብ ድልድሉ ሲወጣ ለዚህ ጨዋታ የማርኬቲንግ ስራዎች መሰራት መጀመሩን ገልፀው የተለያዩ ካምፓኒዎች ጥያቄዎችን አቅርበው ሴፍዌይ ከሚባል ተቋም ጋር ስምምነት መፈፀሙን ተናግረዋል።
በዚህም ፌዴሬሽኑ ለአርብ ለሊቱ የግብፅ ጨዋታ ብቻ 70 ሺህ ዶላር ገቢ ያገኛል ብለዋል።
አቶ ባህሩ በዛሬው መግለጫቸው ከሰሞኑ በስፋት ወደ መጠናቀቁ ስለመቃረቡ እየተነገረ ስለሚገኘው ባህርዳር ስታዲየም ጋር በተያያዘ ለተነሳላቸው ጥያቄ ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
የባህርዳር ስታድየም ግንባታ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የክለብ ላይሰንሲንግ ክፍል ሰፊ ክትትል እየተደረገበት ያለ ነው ሲሉ ዋና ስራ አስፈፃሚው ተናግረዋል።
“የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በተለያዩ ጊዜያቶች የሰጣቸው ግብረ መልሶችን በአግባቡ ተከትሎ በመናበብ እየተሰራ ያለ ስታድየም ቢኖር የባህርዳር ስታድየም ነው።”
አክለውም የባህርዳር ስታድየምን የካፍ እና የፊፋን መስፈርቶች አያሟላም ብሎ ያገደው የቀድሞው የካፍ የክለብ ላይሰንሲንግ ኃላፊ መሀመድ ሲዳት እየተሰራ ባለው ስራ መደነቁን ገልፀዋል።
“መሐመድ ሲዳት እየተሰራ ባለው ስራ ተደንቆ ፤ ስራው በዚህ ደረጃ የሚቀጥል ከሆነ በቀጣይ አምስት ወራት ውስጥ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሀገሩና በደጋፊው ፊት መጫወት የሚችልበት ዕድል አለው ብሎ በእርግጠኝነት የተናገረበት ነው።”
ሌሎችም በሀገሪቱ የሚገኙ ስታድየሞች የባህርዳር ስታድየም ተሞክሮ እንዲወስዱ እና ብሔራዊ ቡድኑ በሀገሩ እዲጫወት እንዲያደርጉ ጥሪ ያደረጉት አቶ ባህሩ ጥላሁን መሀመድ ሲዳት በግላቸው የአማካሪ ድርጅት አማካይነት ሌሎችንም ስታድየም ጎብኝተው ለፌዴሬሽኑ ሪፖርት አቅርበዋል ብለዋል።
መሀመድ ሲዳት የአደይ አበባ ፣ የባህር ዳር ፣ የአዲስ አበባ ፣ የድሬዳዋ ፣ የጅማ ዩኒቨርስቲ እና የአቃቂ ቃሊቲ ስታድየሞችን ጎብኝተው ለፌዴሬሽኑ ሪፖርት ማስገባታቸውንም ጠቅሰዋል።
ከነዚህ ስታድየሞች መካከል የአደይ አበባ ፣ የባህርዳር እና የአቃቂ ቃሊቲ ስታድየሞች ደረጃቸውን ጠብቀው እየተሰሩ ያሉት ናቸውም ብለዋል።
በተጨማሪም ከስታዲየም ፋሲሊቲዎች ጋር በተያያዝ ፌዴሬሽኑ ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ጋር በጋራ በመሆን በደንብ የሚከተታል የጎደሉ ነገሮችን እየተመለከተ ግብረ መልስ የሚሰጥ ኮሚቴ መቋቋሙን ገልፀዋል።


