*…. ዋነኞቹ ባለድርሻ የሆኑት ክለቦች ዕጩ ፕሬዝዳንት እንዳያቀርቡ ታግደው ክለብ አልባ ለሆኑት የክፍለ ከተሞች መፈቀዱ ቅሬታ ፈጥሯል…
*…. የጽ/ቤት ሃላፊው ማስጠንቀቂያ ተሰጠው….
የአዲስ አበባ ከተማ እግርኳስ ፌዴሬሽን ጠቅላላ ጉባኤ ስልጣን በሰጠው የደንብ ሰነድ አዘጋጅ ኮሚቴ የስራ ድርሻ ላይ ጣልቃ እየገባ ነው በሚል የአ/አ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ላይ ቅሬታ ቀረበ።
የጠቅላላ ጉባኤው የከተማውን እግርኳስ ዕድገት ላይ ማነቆ በሆኑና በደንቡ ላይ መካተት ያለባቸውን ህጎች አካቶ ለማጸደቅ ጥናት አድርጎ እንዲያቀርብ ስልጣን በሰጠው አካል ላይ ቢሮው ጣልቃ እየገባ አላሰራ ብሏል የሚል ቅሬታ ከተወከለው ኮሚቴ መቅረቡ ተሰምቷል።
- ማሰታውቂያ -
ፌዴሬሽኑ ደንብና የምርጫ ሰኘድ ላይ ካልነበሩትና አጠቃላይ እግር ኳስን በሚመሩ አካላት የማይጠፉ የፍትህ አካላት ፣ የኦዲት ኮሚቴና የይግባኝና ግልግል ኮሚቴ የሌለው መሆኑ እግርኳሱ ላይ ከፍተኛ ሚና ያላቸው የተጨዋቾች ፣ የአሰልጣኞች የዳኞችና ኮሚሽነሮች ማህበራት ድምጽ የሌላቸው መሆኑ ሲያነጋግር የነበረ ክፍተት መሆኑ ይታወቃል። የሰነድና አዘጋጅ ኮሚቴው እነኚህንና የጠቅላላ ጉባኤው የተፈጻሚነት ወሰን የሚለውን በሰነዱ ላይ አካቷል።
ነባሩና በ2013 የጸደቀው ደንብ ከዚህም ውጪ በእግርኳስ ፌዴሬሽኑ ውስጥ በሚካሄዱ የትኞቹም ውድድሮች ላይ የማይወዳደሩት ክፍለ ከተሞች ብቻ ለፕሬዝዳንትነት እጩ እንዲያቀርቡ ዋነኛ ባለድርሻ የሆኑትና ክለቦች ግን ስራ አስፈጻሚ እንጂ ዕጩ ፕሬዝዳንትን እንዳይልኩ የከለከለ ሲሆን በአዲሱ ደንብ ላይ ግን ክለቦች ዕጩ ስራ አስፈጻሚም ሆነ ፕሬዝዳንት እንዲልኩ ተደርጎ የተስተካከለ ቢሆንም ከላይ የተጠቀሱትን አዲሶቹ ደንቦችን ቢሮው በማህበራት ማደራጃ ዳይሬክቶሬት በኩል ከደንቡና መመሪያው ሰርዞ የሰነድ አዘጋጁን ልፋት ገደል ከትቷል በሚል ወቀሳ ቀርቦበታል።
የፍትህና የኦዲት ኮሚቴዎች በጠቅላላ ጉባኤው የሚመረጡና ቀጥተኛ ተጠሪነታቸው ለጠቅላላ ጉባኤው ብቻ እንጂ በፌዴሬሽኑ አመራሮች የማይጠየቁና የማይታዘዙ ዋነኛ ኮሚቴ መሆናቸው እየታወቀ ቢሮው አይሆንም ማለቱ እግር ኳሳዊ አመራር ላይ ያሐውን ክፍተት ያሳያል ተብሏል።
ጉዳዩን የሚከታተሉ ባለሙያዎች ግን የቢሮው ጣልቃ ገብነት ህገወጥ መሆኑን በመግለጽ ጠቅላላ ጉባኤ የወከለውን አካልና የግድ በሰነዱ ሊካተቱ ይገባል የተባሉ አንቀጾችን ሰርዞ መላኩ ከብሄራዊ ፌዴሬሽኑ ጋር እንዳያጋጨውና የስፖርቱን ዘርፍ የሚመራው አካልና ማህበራት ማደራጃው የእውቀት ማነስ የሚታይበት መሆኑ ቢሮውን ለትዝብት ይዳርጋል እያሉ ስጋታየውን እየገለጹ ነው። የየክፍለ ከተሞቹ ስራ አስፈጻሚውች ይህን ሴራ ያውቁ ይሆን ..? የሚሉት ባለሙያዎቹ በትውውቅና በውስጥ ለውስጥ አሰራር በየክፍለ ከተማዎቹ የሚወከሉ ሰዎች በትክክል አቅም ያላቸው መሆናቸው መረጃው አላቸው ወይ ..? እንዲልኩ የማይፈቀድላቸው ክፍለ ከተሞችስ ለምን ብለው ይጠይቃሉ..? የአሁኑ ምርጫ ላይ ተወካይ የላኩት ከ3 የማይበልጡ መሆናቸውንስ ይረዱት ይሆን ..? ብለው ጠይቀው በየክፍለ ከተማዎቹ ያሉትን ወጣቶችን ለቅሬታ የሚዳርገውን ሂደት እንዲያስቀለብሱ ዋና ስራ አስፈጻሚዎቹን ጠይቀዋል።
ከወራቶች በፊት ከትውልደ ኢትዮጵያዊያን ጋር ተያይዞ ከከተማው አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ጋር ውዝግብ ውስጥ የነበሩት ቢሮውና የማህበራት ማደራጃው አሁን ከእግርኳስ ፌዴሬሽኑ ጋር አለመግባባት መፍጠራቸው ልዩነቱ ሌላ አቅጣጫ እንዳይይዝ የብዙዎች ስጋት ሆኗል።
በሌላ በኩል ያለ ፌዴሬሽኑ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ዕውቅናና ስልጣን ውጪ በራሱ የግል ውሳኔ የፌዴሬሽኑን ጠቅላላ ጉባኤ ግዮን ሆቴል እንዲደረግ ከሆቴሉ ጋር የተነጋገረው የጽ/ቤት ሃላፊው አቶ አበበ ድረስ ማስጠንቀቂያ ተሰጠው።
የቢሮው ውክልና ያለው የጽ/ቤት ሃላፊው በተደጋጋሚ ጊዜያት የፌዴሬሽኑ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በማያውቀው ሁኔታ በግሉ እየወሰነ ከስራ አስፈጻሚው የቃል ማስጠንቀቂያ ሲደርሰው እንደነበር ታውቋል። ከሰሞኑ ይህን ድርጊት ቀጥሎበት ጠቅላላ ጉባኤው ህዳር 21 ይደረጋል በማለት ከግዮን ሆቴል ጋር በደብዳቤ ምልልስ ማድረጉ ስራ አስፈጻሚውን ያስቆጣ ሲሆን የጽ/ቤት ሃላፊው ከድርጊቱ እንዲቆጠብ የጀመረውን ግንኙነት እንዲያቆም ያ የማይሆን ከሆነ ለሚደርሰው የህግ ተጠያቂነት ሃላፊነቱ የርሱ መሆኑን በመግለጽ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጠው ከታማኝ ምንጭ የተገኘው መረጃ ያስረዳል።


