“ጨዋታው ለኛ የሞት ሽረት ፍልሚያ እንደሆነ እንረዳለን፤ ማለፍና መውደቃችን የሚወሰነው በዛሬው ጨዋታ ነው፡፡”
“ጨዋታው መረጋጋትን እንዲሁም ታጋይነትን ይጠይቃል። ይህን ሁሉ ለማድረግ አምነን ነው ዛሬ ወደሜዳ የምንገባው።”ካሙ ማሎ /የቡርኪናፋሶ ዋና አሰልጣኝ/
ይህን ያሉት የዛሬ ተጋጣሚያችን የቡርኪናፋሶ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ካሙ ማሎ ናቸው፡፡በኮቪድ 19 የተነሳ እስካሁን ድረስ ሙሉ ተጫዋቾቻቸውን ማግኘት ያልቻሉት ካሙ ዛሬም የክለቡን ዋና ግብ ጠባቂ ሄርቬ ኩዋኩ ኮፊን አገልግሎት ማግኘት አይችሉም፤ እርሳቸውም ቢሆኑ ቡድናቸው የመጀመሪያውን ጨዋታ ከካሜሮን ብሔራዊ ቡድን ጋር ሲያደርግ ካሙ በኮቪድ ምክንያት ራሳቸውን አግልለው ከሆቴላቸው በቴሌቪዥን ነው ጨዋታውን የተመለከቱት፡፡
« የዛሬው መልካም ዜና አምበላችን በርትሮ ትራኦሬ ከቫይረሱ ነጻ መባሉ ነው፡፡ ዛሬ መሰለፍ ይችላል፤ በተጨማሪም ሁለቱንም ጨዋታዎች ማቆያ ውስጥ የነበሩት ዳንጎ ዋታራ፣ ሱማይላ ዋታራ እና ሳይዱ ሰምፖሬ ከቫይረሱ ነጻ ተብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ ግብ ጠባቂያችን ሄርቬ ኩዋኩ ኮፊ ዛሬ ግልጋሎት ሊሰጠን አይችልም፡፡» ካሙ ጨምረው እንደገለጹት እንዳለመታደል ሆኖ የሄርቬን አገልግሎት ዛር ልናገኝ አንችልም ብለዋል፡፡
- ማሰታውቂያ -
ተጋጣሚያቸውን በሚመለከት አስተያየት የሰጡት ካሙ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወደካሜሮን የመጣው ለቱሪዝም እንዳልሆነ እናውቃለን ብለዋል፡፡ በወረቀት ላይ ትላልቅ ቡድኖች ብለህ የምታስቀምጣቸው ሃገራት በዚህ የአፍሪካ ዋንጫ በደረጃ በብዙ የሚቀድሟቸው ቡድኖች ማሸነፍ ሲቸገሩ አይተናል፡፡ ሁሉንም ብሄራዊ ቡድን ማክበር ያስፈልጋል፡፡ ጨዋታው ቀላል እንደማይሆን እገምታለው ለኛ ግን ማሸነፍ ግዴታችን ነው፡፡
የሁለቱ ሃገራት ጨዋታ ዛሬ ምሽት አንድ ሰዓት በባፉሳም ከተማ ኩኮንግ ስታዲየም የሚደረግ ሲሆን ሁለቱ ሃገራት ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት በደቡብ አፍሪካው የአፍሪካ ዋንጫ ሁለተኛ ጨዋታ እንደነበር ይታወሳል፤ ድል ለዋልያዎቹ !