በያዝነው የውድድር ዘመን ወላይታ ድቻን የሚመራው ሦስተኛው አሰልጣኝ ታውቋል።
ሀያ ቡድኖችን በሚያሳትፈው የ2018 የውድድር ዘመን የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አራቱን ተሸንፎ በአንዱ ነጥብ በመጋራት በደረጃ ሰንጠረዡ ግርጌ ላይ የተቀመጠው ወላይታ ድቻ አሰልጣኝ ገብረክርስቶስ ቢራራን ከአራት የሽንፈት ጉዞ በኋላ በማሰናበት ረዳት አሰልጣኙ ቴዎድሮስ ቀነኒን በጊዜያዊ መንበሩ ሾሞ ከመቐለ 70 እንደርታ ጋር 2ለ2 ከተጠናቀቀው ጨዋታ በኋላ የመስራት ነፃነትን አጣሁ በማለታቸው ከጊዜያዊ አሰልጣኙም ጋር ክለቡ መለያየቱ ይታወሳል።
ይሁን እንጂ ክለቡ አሰልጣኝ ለመቅጠር ሰፋ ያለ ጊዜን ማስፈለጉን በመገንዘብ ከሀዋሳ ከተማ የተስፋ ቡድኖች ጀምሮ እስከ ዋናው ቡድን ድረስ የግብ ጠባቂ እንዲሁም ረዳት አሰልጣኝ በመሆን ጭምር ከአስራ ስድስት አመታት በላይ ያገለገለውን በኋላም በካፋ ቡና በከፍተኛ ሊጉ በማሰልጠን ቆይታን ያደረገው እና በወላይታ ድቻ የአካል ብቃት አሰልጣኝ እያገለገለ የነበረው አሰልጣኝ አምጣቸው ሐይሌ የኤ ላይሰንስ (ሪፍሬሽመንት ኮርስ ይቀረዋል) ባለቤት መሆኑን ተከትሎ በሚያሳየው ውጤት መሠረት ጊዜያዊ የጦና ንቦቹ አሰልጣኝ በመሆን በዓመቱ የክለቡ ሦስተኛው አሰልጣኝ ሆኖ መሾሙን ሀትሪክ ስፖርት አረጋግጧል።
ወላይታ ድቻ የፊታችን ዕርብ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን በአዲስ አበባ ስታዲየም በስድስተኛው ሳምንት መርሀ ግብር የሚያስተናግድ ይሆናል።


