ስመ ጥሩ የአዲስ አበባ ስታዲየም ዕድሳት ተደረገለት ቢባልም ከእንከኖቹ ግን መላቀቅ አልቻለም።
ከኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ እስከ አፍሪካ ዋንጫ በሴካፋ ስር ከሚደረጉ የዋናው እና የተለያዩ የዕድሜ ዕርከን ቡድኖች በሁለቱም ፆታ ከንጉሱ ዘመነ መንግስት እስከ ቅርብ ጊዜያት ወዲህ ውድድርን በማሰናዳት ስሙን በታሪክ ማዕደር ውስጥ አስፍሯል ፣ የሀገሪቱን ትልቁን የደርቢ ጨዋታ ጨምሮ ፣ የፕሪምየር ሊጉን የዋንጫ ፍክክሮች ፣ ኢትዮጵያ በአፍሪካ እና በሴካፋ ያገኘቻቸውን ዋንጫዎች ከፍ አድርጋ ያነሳችበት ታሪካዊ ስታዲየም ነው የአዲስ አበባ ስታዲየም። 2013 ላዮ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ በክለቦች መተዳደር በጀመረበት ወቅት የሊጉን የመጀመሪያ አምስት የጨዋታ ሳምንታትን ካሰናዳ በኋላ ለዕድሳት በሚል ለአራት አመታት አንድም ውድድርን ሳያስተናግድ ፆሙን የከረመው ይህ አንጋፋ ስታዲየም ተደረገለት ከተባለው ዕድሳት መልስ የዘንድሮውን የ2018 ፕሪምየር ሊግ በማስተናገድ ወደ ቀደመ ዝናው መመለስ ቢችልም ስታዲየሙ ግን ለስም ታደሰ ከሚለው ማዕረግ ውጪ አሁንም አሳሳቢ ደረጃ ላይ እንዳለ ሀትሪክ ስፖርት ለመታዘብ ችላለች።

- ማሰታውቂያ -
በባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አማካኝነት መጀመሪያ ላይ 38 ሚሊዮን ተሻሽሎ ደግሞ 110 ሚሊዮን በመጨረሻም ሦስት ፐርሰንት ቀሪ ዕድሳት አለው በሚል ወደ 150 ሚሊዮን ገንዘብ ፈጀ ተብሎ የተነገረለት ይህ አንጋፋ ስታዲየም ከሚታዩት የቪአይፒ ክፍሎች እና የመወጣቻ ሊፍቱ በቀር መቀመጫ ወንበሮቹ በድጋሚ ተሰባብረው ከጥቅም ውጪ ሲሆኑ በዘመናዊ መልኩ እየተነጠፈ ነው ሲባል የነበረለት የመጫወቻ ሳሩም ዶግ አመድ ወደ መሆን እየተለወጠ መሆኑን ታዝበናል። የኢትዮጵያ ዋንጫ ከሰሞኑ እየተደረገ በጨዋታዎች መሐል በተሰባበሩ ወንበሮች ምትክ ሌላ ሲገጠም ያስተዋልንበት ስታዲየሙ በቀጣይ ዕድሳት እንኳን ቢኖረው ምንም ኢንቨስት እንደማያደርግ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር ዲኤታው አቶ መኪዩ መሐመድ በቅርቡ መናገራቸውን ተከትሎ አሁንም ከእንከኖች ፈቅ ያላለው ስታዲየም ዕጣ ፈንታው አሳሳቢ መሆኑ የሚቀር አይመስልም።


