አላስፈላጊ ካርዶች እና መሻሻል የሚገባው የተጫዋቾች የዲሲፕሊን ግድፈት …!
ተስፋን የሰነቁ ወጣት ተጫዋቾች እና አዳዲስ ፊቶች…!
ካለፈው አመት መማር ያልቻሉ እና ኮስተር ብለው የተመለሱ ክለቦች…!
የቡድን ግንባታ ልልነት.. ወጥ ያልሆነ አቀራረብ …የታክቲክ ውስንነት….!
- ማሰታውቂያ -
የዳኞች ብቃት ማነስ እና መፍትሄው …!

የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አክሲዮን ማህበር ከተቋቋመ ስድስተኛ ዓመቱን ደፍኗል። ሊጉ ራሱን ችሎ በክለቦች መተዳደር ከጀመረ ወዲህ ባልተለመደ መልኩ የቀጥታ የቴሌብዥን ሽፋን እና ክለቦችም ዓመቱ መጨረሻ ላይ የገንዘብ ስጦታን እያገኙበት ላለፉት አምስት አመታት ቆይታን ማድረጉ ይታወሳል። ከዲኤስቲቪ ጋር በኮንትራት መቋጫ መልስ ወደ ሀገር ውስጥ የቴሌብዥን ጣቢያ ፊቱን በማዞር በስድስተኛ ዓመቱ በኦቢኤን የቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭትን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ደግሞ መጠሪያውን የሸጠው ሊጉ በሀያ ክለቦች ከጥቅምት 8 ጀምሮ ከአራት ዓመታት በኋላ በአዲስ አበባ ስታዲየም እና ለተከታታይ አምስት አመታት ደግሞ ሲደረግበት በነበረው የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ስታዲየም የሀገራችን ትልቁ የሊግ ዕርከን የ2018 የውድድር ዘመኑን ፈጠን ባለ ፎርማት አምስት ሳምንታትን አሳልፎ ለኢትዮጵያ ዋንጫ እና ክለቦች በሚኖራቸው የከተማ ለውጥ ምክንያት ለቀናት ዕረፍትን በማድረግ ከቀጣዩ ሳምንት ህዳር 11 ጀምሮ በስድስተኛ ሳምንቱ የሚመለስ ሲሆን እኛም የታዘብናቸውን ትኩረት ሳቢ ጉዳዮችን እናነሳለን።
አላስፈላጊ ካርዶች እና መሻሻል የሚገባው የተጫዋቾች የዲሲፕሊን ግድፈት …!
በአምስት የውድድር ሳምንታት ውስጥ (ኢትዮጵያ መድን ከቅዱስ ጊዮርጊስ እና ሸገር ጋር ያለውን ተስተካካይ ጨዋታዎች ሳያካትት) 48 ጨዋታዎች የተደረጉበት ሊጉ በሜዳ ላይ የጎለበቱ ፉክክሮችን ብናስተውልም በዋናነት የዲሲፕሊን ጉድለቶች ጥፋቶች እና በርካታ ካርዶችን ያስተዋልንበት ነበር። እስከ አሁን በተደረጉ አርባ ዘጠኝ ጨዋታዎች 247 ቢጫ ካርዶች እና 12 ቀይ ካርዶች (ሦስት ቀጥታ ቀይ) ተጫዋቾች እና አሰልጣኞች የተመለከቱ ሲሆን ከጥፋቶች ባሻገር የተሰጡት አብዛኛዎቹ ካርዶች ከዳኛ ጋር አላስፈላጊ ግጭት ውስጥ በመግባት ያገኟቸው እንደሆነ ልብ ሊባል ይገባዋል። ከዚህም መነሻነት ሊጉ ሲመለስ የዲሲፕሊን ጉዳዮች ላይ ከሜዳ ላይ ተፎካካሪነት በዘለለ ክለቦች አሻሽለው ሊመለሱ እንደሚገባቸው መናገር ያሻል። በሌላ በኩል ደግሞ ተጫዋቾች ጥፋት ሰርተው ካርዶችን ማየት ሲችሉ የተለመደ ቢሆንም የሚሰሩ ጥፋቶች ግን አደገኛ ከመሆናቸው አንፃር እንዲሁም ተስፋ የሚጣልባቸውን ተጫዋቾች በዚህ የተነሳ ልናጣ ስለምንችል ጥንቃቄ እና ትኩረት መሰጠት እንዳለበት ጭምር ለመጠቆም እንወዳለን።
ተስፋን የሰነቁ ወጣት ተጫዋቾች እና አዳዲስ ፊቶች…!
በይበልጥ ተመሳሳይ ፊቶችን በየአመቱ የምናስተውልበት ሊግ ይህኛው አመት ግን በመጠኑም ቢሆን በአዳዲስ ፊቶች የተሞላ በረከትን እንካቹ ብሎናል። በፋይናንስ ህጉ ጥብቅነት የተነሳ ቡድኖች ወደ ወጣት ቡድናቸው እና ወደ ታችኛው የሊግ ዕርከኖች መመልከት መጀመራቸውን ተከትሎ ከአምናው በላቀ ቁጥር አዳዲስ ፊቶችን ገና በአምስት ሳምንታቶች ውስጥ አጉልቶ ማሳየትን ጀምሯል። ለሀዋሳ ከተማ አራት ጎሎችን ከመረብ ያሳረፈው ወጣቱ አማካይ ያሬድ ብሩክ እና የአብስራ ደግፌ ፣ የቅዱስ ጊዮርጊሶቹ ሀብታሙ ጉልላት ፣ ቯይ ኩዌት ፣ ያብስራ ጎሳዬ እና መሳፍንት ፓውሎስ ፣ የባህር ዳሩ ማንያዘዋል ካሳ ፣ የኢትዮጵያ ቡናው ሚኪያስ በዳሶ ፣ የኢትዮጵያ መድኑ ዳዊት አውላቸው ፣ የነገሌ አርሲዎቹ ከቤ ብዙነህ እና ሮቦት ሰለሎ ፣ የሸገር ከተማዎቹ ያሬድ መኮንን ፣ ምስጋና ሚልኪያስ እና አቤኔዘር ሕዝቄል ፣ የኢትዮ ኤሌክትሪኩ ሀሰን ሁሴን እና ሌሎች በቋሚነትም ይሁን በቅያሪ መልክ ከተስፋ ቡድን እና ከከፍተኛ ሊጉ እንዲሁም ከአንደኛ ሊጉ ብቅ ያሉ ተጫዋቾች በሊጉ ያለፈውን አምስት ሳምንታት ለቡድኖቻቸው ጥሩ ግልጋሎት እየሰጡ ለመመልከት ችለናል።
ካለፈው አመት መማር ያልቻሉ እና ኮስተር ብለው የተመለሱ ክለቦች…!
ዘንድሮው ፕሪምየር ሊጉ የሰላሳ ስምንት ሳምንት ርዝማኔ ያለው ከመሆኑ አኳያ ክለቦች በዝግጅት ወቅት ቡድናቸውን በሚገባ ደፍነው ለውድድር ብቁ ሆነው መገኘት ቢገባቸውም በተጠናቀቀው የውድድር ዘመን የቁልቁል ሲጓዙ የነበሩ ክለቦች አሁንም ከዳፋው መላቀቅ ተስኗቸው በተመሳሳይ የውጤት ርሀብ ውስጥ ዘንድሮም መገኘት መቻላቸው አግራሞትን ጭሯል። መውረድ ኖሮ ቢሆን ላንመለከታቸው የምችላቸው መቐለ እና ወልዋሎ ባለፈው ዓመት ቆመው ከነበረበት የቀጠሉ ይመስላል። አዳዲስ አሰልጣኞችን በመንበራቸው አምጥተው የበርካታ ተጫዋቾችን ግዢ ፈፅመው ወደ ውድድር ቢገቡም አንድም ጨዋታ ማሸነፍ ተስኗቸው በደረጃ ሰንጠረዡ የመጨረሻው ስፍራ ላይ መቀመጥ የቻሉ ሲሆን እንደ ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ፋሲል ከነማ አይነቶቹ ደግሞ ተሻሽለው ብቅ ብለዋል። ወጣቶችን በማሳደግ የሚታወቀው እና ዘንድሮ ሊጉ የከቀደው ወላይታ ድቻ ፣ አርባምንጭ ከተማ እና ሀድያ ሆሳዕና ወደ ተፎካካሪነት ለመመለስ ብዉ የቤት ስራዎችን ሰርተው ሊመለሱ ግድ ይላቸዋል። እንደ ኢትዮጵያ ቡና አዲስ አዳጊዎቹ ሸገር እና ነገሌ ፣ ንግድ ባንክ ፣ ባህርዳር እንዲሁም ሽረ ምድረገነት የተጫዋችነን የሜዳ አጠቃቀም ሚናን ማጎልበት እንደ መቻል ፣ ሲዳማ ቡና ፣ ሀዋሳ ከተማ ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ድሬዳዋ ከተማ በበኩላቸው ከወገብ በታች የሚገኘው ቦታቸው ላይ እርምትን መውሰድ የሚገባቸው ሲሆን በተለይ ሀዋሳ እና ድሬዳዋ ግን እንደ ቡድን ንቃት የሚያስፈልጋቸው ቡድኖች እንደሆኑ መታዘብ የቻልን ሲሆን ሁለት ተስተካካይ ጨዋታ የሚጠብቀው ኢትዮጵያ መድን በአንፃሩ በቻምፒየንስ ሊጉ ካጣው ትኩረት የሚመለስ ከሆነ ወደ አምናው የስኬት መንገድ መንደር ይችላል።
የቡድን ግንባታ ልልነት.. ወጥ ያልሆነ አቀራረብ …የታክቲክ ውስንነት….!
ገና ከመጀመሪያው ሳምንት ጀምሮ ክለቦች በታክቲክ ዕሳቤ ዳብረው ከመቅረብ ይልቅ ዱላ ቀረሽ አጨዋወትን ይዘው በመቅረብ ተመልካቹ ማየት ከሚገባው ኳሳዊ ባህሪ ይልቅ ተደጋጋሚ ጥፋቶችን አለፍ ሲልም አሰልቺ እንቅስቃሴዎች እንዲበራከቱ ፣ ፍላጎትን እንጂ ወጥ የሆነ የጨዋታ መንገድን ከውስን ክለቦች ውጪ መመልከት አልቻልንም። ለዚህም በዋናነት ክለቦች ያሏቸውን ተጫዋቾች በማቆየት ጥቂት ግዢን ብቻ ፈፅመው ቡድን ግንባታቸውን ከማሳደግ ይልቅ ክረምት በመጣ ቁጥር በጅምላ ይህም ማለት ከአስር በላይ ተጫዋቾችን በማስፈረም ወጥ የሆነ ቡድንን ይዘው እንዳናይ መሆኑ ከጨዋታ ጨዋታ ወጥነት የጎደለውን እንቅስቃሴ እንዲያሳዩ መገደዳቸው በማጥቃት ወቅትም የሚቆራረጡ ኳሶች መበራከታቸው በዚህም የተነሳ በቂ የጎል ዕድሎች ሲፈጠሩ አለማስተዋላችን ቡድኖች በታክቲክ የጎለበት ስታንዳርዱን የጠበቀ ማንነታቸውን ከውስን ክለቦች ውጪ ይዘው አለመቅረባቸውን ያለፉት የጨዋታ ሳምንታቶች በይበልጥ ያስመለከቱን ችግሮች መሆናቸውም ታዝበንበታል።
የዳኞች ብቃት ማነስ እና መፍትሄው …!
የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ባለፉት ከጥቂት አመታቶች ወዲህ አዳዲስ እንዲሁም በሜጃ ላይ አቅማቸው ከፍ ያሉ ወጣት ዳኞችን እያሳየን ይምጣ እንጂ የህግ ክፍተት እና የውሳኔ ልልነት ያለባቸውን ዳኞች በተመሳሳይ እያየንበት እንደገኛለን። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽን የዳኞች ኮሚቴ ከተለመደው የዳኝነት የስልጠና አሰጣጥ ወጣ በማለት በተለያዩ የሀገሪቱ ክለቦች ለወጣት እና ታዳጊ ዳኞች ተከታታይ የዘመነ ስልጠናን በመስጠት የላቁ ዳኞችን ለማፍራት እየሄደበት ያለው ርቀት እና ለረጅም አመታትም ይዞታ በሚመስል መልኩ የኢንተርናሽናል ባጅን ይዘው ሀገራችንን ማስጠራት ባልቻሉት ምትክ ወጣቶችን ማብቃቱ የሚያስመሰግነው ተግባር መሆን ቢችልም በአዲስ አበባ እና ሀዋሳ የታዘብናቸው አንዳንድ ዳኞች ግን እርምት ሊወሰድባቸው ይገባል። አራት ቡድኖች የሚወርዱበት ረጅም የጨዋታ ሳምንታቶችም ከመኖራቸው አንፃር ዳኞች በአካልም ሆነ በአዕምሮ አድገው ሜዳ ላይ ከሚያሳዩት ደካማ የዳኝነት አቅም እንዲሻሻሉ ኮሚቴው በቀጣይ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል።


