በበርካታ ፈተናዎች ውስጥ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ አራተኛ ከሳሹ ቶጓዊው አጥቂ ሆኗል።
ባሳለፍነው የውድድር ዘመን ለቅዱስ ጊዮርጊስ ግልጋሎት እየሰጠ የነበረው ቶጓዊው አጥቂ ሳሚዮ ታቺታኮራን ቅዱስ ጊዮርጊስ ያልከፈለኝ ገንዘብ አለ በተደጋጋሚ ብጠይቅም መልስ ባለ መስጠቱ ክለቡን ለፊፋ ከስሻለሁ ሲል ተጫዋቹ ካለበት ቡሩኪናፋሶ አሳውቆኛል። ለሀገሩ አራት ክለቦች ከተጫወተ በኋላ ለቤኒኑ በኬን በኋላም ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ ከመምጣቱ በፊት ለሊቢያው ሴንት ኤሎይ ሉፓፓ በመጫወት ያሳለፈ ሲሆን አጥቂው ወደ ሀገራችን መጥቶ ቅዱስ ጊዮርጊስን በሁለት አመት ውል ተቀላቅሎም ከሀገራችን እግር ኳስ ጋር መተዋወቅ ቢችልም በክለቡ ብዙም አመርቂ ጊዜን ሳያሳልፍ መለያየት ችሏል።
ከአንድ አመት በላይ ያልተከፈለ ገንዘብ አለኝ የሚለው እና ከ14 ቀናት በፊት የቡሩኪናፋሶውን ራሂሞን ክለብ በይፋ የተቀላቀለው አጥቂው ከጋናዊው አማካይ ኩዋሜ ፍሪምፓንግ ፣ ከአይቮሪያኑ አጥቂ መሐመድ ኮኔ እና ከዩጋንዳዊው ተከላካይ ጊፍት ፍሬድ ቀጥሎ ክለቡን የሰሰሰ አራተኛው ተጫዋች ሆኗል።
በተጫዋቾቹ በመከሰሱ የተነሳ በዝውውር እንይሳተፍ የታገደው አንጋፋው ክለብ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከባድ ፈተናዎችን እያሳለፈ የሚገኝ ሲሆን ከደመወዝ ክፍያም ጋር በተያያዘ በአሁኑ ሰዓት የክለቡ ተጫዋቾች ቅሬታ ላይ እንደሚገኙ ለማወቅ ችያለሁ። በሌላ በኩል ደግሞ በክለቡ አዲስ የተመረጡ ቦርዶችም በተጣለባቸው የፍርድ ቤት ዕግድ እና ሌሎች ከገንዘብ ጋር ያሉ ችግሮች ክለቡን መፈተናቸውን ቀጥሏል።


